የኢትዮጵያ ፖለቲካ – ፲ ፱ ፻ ፹ ፫ እንደገና

የኢትዮጵያ ፖለቲካ – ፲ ፫ እንደገና

የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር የጫነብን የዘር ክልል አስተዳደር፤

 

አሁን ለተዘፈቅንበት የፖለቲካ አረንቋ ምክንያቱ ነው? ወይንስ መፍትሔው?

አንዱዓለም ተፈራ፣ ረቡዕ፣ መስከረም ፲ ፮ ቀን፣ ፳ ፻ ፲ ፩ ዓ. ም. (Wednesday, September 28, 2018)

ሀገራችን አሁን በአስጊ መስቀለኛ መንገድ ላይ ትገኛለች። በዓለም ዙሪያ ተደናቂነትን ያገኘው አሁን የተጀመረው የለውጥ ሂደት፤ ከፍተኛ አደጋ አንዣቦበታል። በፖለቲካ መድረኩ ላይ እየተጫወቱ ያሉት አንዳንድ ድርጅቶች፤ አጀንዳውን ወደየ ፍላጎታቸው እያንጋደዱ ለመውሰድ፤ የለውጡን ሂደት ስጋት ላይ የጣለ፤ ግብግብ ላይ ናቸው። ይህ የሀገራችንን ሕልውና በንጥልጥል አስቀምጦታል።

ግንቦት ፲ ፱ ፻ ፹ ፫ ዓመተ ምሕረት፤ ሶስት ነፃ አውጪ ግንባሮች፤ ከኤርትራ፣ ከትግራይ እና ከኦሮምያ፤ የሰው በላውን አምባገነን መንግሥቱ ኃይለማርያም ሥልጣን ወረሱ። ከዚያ ጊዜ ጀምሮ፤ እኒህ ሶስቱ ድርጅቶች፤ ሀገራችን ላለፉት ሃያ ሰባት ዓመታት ያለፈችበትን ሂደት ወስነውታል። የኤርትራዊያን ነፃ አውጪ ግንባር (ህግሓኤ)፤ በቀሪዎቹ በሁለቱ ድጋፍና እውቅና፤ ሀገሪቱን በመገንጠልና ወደብ አልባ በማድረግ፤ የራሱን ሀገር መሠረተ። የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር (ትሕነግ) እና የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)፤ ባጣዳፊ የፈለጉትን የዘር ክልል ፌዴራሊዝም በኢትዮጵያ መሠረቱ። የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር፤ የሀገሪቱን 6% ብቻ የሚሆኑትን ትግሬዎችን እወክላለሁ በማለት፤ ቀሪውን 94% የሚሆነውን የሀገሪቱን ወገን ለመግዛት፤ አመቺ የሆነ ሕገ-መንግሥት በቦታው ማስቀመጥ ነበረበት። በሜዳ ውስጥ የኳስ አቀባይነት ሚና የተጫወተው የኦሮሞ ነፃነት ግንባር፤ የሥልጣን ጉርሻ አገኛለሁ በማለት፤ ጓጉቶ ተሳተፈ።

የኦሮሞ ነፃነት ግንባር መሪዎች፤ አንድም ዕውቀቱ ጎድሏቸው ነበር፤ አለያም በትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር የተመሠረተው የኦሮሞዎች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) ይጠፋል! ወይንም በኦሮሞዎች ፊት በሚደረገው ምርጫ፤ የሕዝቡን ልብና አእምሮ እኛ እንወስዳለን! ብለው አምነው ነበር። ነገር ግን፤ ኦነግ በሁለቱም በኩል ባዶ ቀረ። ጨካኙ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር፤ ይህ እንዲሆን ብቻ ሳይሆን፤ ኦነግን ለማጥፋት፤ ቀን ተሌት ተሯሯጠ። እናም ያንኑ ድርጊት፤ በሺዎች የሚቆጠሩ ኦሮሞዎችን በመግደልና በአስርት ሺዎች የሚቆጠሩትን ለእስር በመዳረግ አጠናቀቀ። በትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባሩ የተመሠረተው ኦሕዴድ፤ በትሕነግ መንግሥት እርዳታና በአካባቢው ባቋቋመው መዋቅር፤ ቀስ እያለ እያደገ ሲሄድ፤ በትሕነግ የተደቆሰው ኦነግ፤ በተለያዩ ምክንያቶች ተከፋፈለ።

በቅርቡ የዐማራና የኦሮሞ ወጣቶች፤ “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግፍና በደል በቃን!” ብለው ተነሱና ይሄ ገዢ ቡድን ሀገሪቱን እንዳፈተተው መግዛት እንዳይችል አደረጉት። አረመኔው ዘረኛ የትሕነግ ገዢ ቡድን፤ በጁ ያገኘውን ማንኛውንም ኢሰብዓዊ ጭፍጨፋ በማከሄድ ሊቆጣጥር ሞከረ። አልተሳካለትም። ይልቁንም ኦሕዴድና ብዐዴን በመካከላቸው ያቆመባቸውን አጥር አፍርሰው፤ ወዳጅነት በመፍጠር፤ ጉልበታቸውን አፈረጠሙ። የቀጥታ ግንኙነታቸውን አጠንክረው፤ ግልጥ የሆነ የአንድነት ዓርማ አውለበለቡ። ከዚያ ቀጥለው፤ አረመኔው ትሕነግ፤ በሕዝቡ ላይ የለቀቀውን ያልተገራ ወታደራዊ እርምጃ፤ መጠየቅ ጀመሩ። የተርበተበተው የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር የቀድሞ አጋሮቹን ከቀበረበት ቦታ መቆፈር ያዘ። በኤርትራ በኩል በማያዳግም ሁኔታ ድሮ ድልድዩን አፍርሷል። በሌላ በኩል፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ በየቦታው ሆ! ብሎ ሲነሳበትና የኢሕአዴግን መሠረት ሲያናጋው፤ የኦሕዴድና የብዐዴን አመራር ለውጥ ፈላጊ ቡድን፤ ከሕዝቡ ጋር ወገነ። በዚያ ሰዓት የሀገሪቱ አመራር በለውጥ ፈላጊዎች እጅ ወደቀ።

በቅርብ ጊዜ፤ በአረመኔ አምባገነን መሪዎች ሥር የነበሩ የተለያዩ ሀገሮች ያደረጓቸውን ለውጦችና ከዚያ የተከተለውን ስንመለከት፤ ምንም ዓይነት ቀመር እንደሌለና ተከታዩ ይሄ ነው ብለን የምንተነብይበት መሣሪያ እንደማናገኝ እንረዳለን። እስኪ አስቡት፤ የምሥራቅ አውሮፓዊያን ሀገራትን የቀለም አብዮት፣ በመካከለኛው ምሥራቅ የአረብ ሀገራት ፀደይና በሊቢያ፣ ግብጥና የመን የተከተለው፣ የአይሲስ መነሳትና ወርዶ መከስከስን ማን ከመከሰታቸው ከጥቂት ዓመታት በፊት ገምቶ ነበር? ይህ ያስተማረን፤ የአንድን ሀገር ክስተት፤ ቀደም ብሎ በመመርመር፤ በታወቀ ቀመር አስገብቶ፤ የሚሆነው እንዲህ ነው ብሎ መገመት አዳጋችነቱን ነው። በያንዳንዱ ሀገር ያለው የኅብረተሰብ ኡደት ወሳኝና የተለያየ ነው። እናም በሀገራችን የሚከተለው ምን እንደሚሆን ማወቁ አስቸጋሪ ነው። ብዙ ሊሆኑ የሚችሉ ሁኔታዎች አሉ። አንዳንዶቹ እንቅልፍ ይነሳሉ። ሌሎች ደግሞ ትንፋሽ ያረጋጋሉ።

እስካሁን የታወቀው ይህ ነው። ለውጥ ፈላጊ በመንግሥት ቁንጮ ላይ ተቀምጧል። ይህ ለውጥ ፈላጊ ክፍል በአብዛኛው ሕዝብ የተፈቀረና የተደገፈ ነው። በመንግሥቱ ውስጥ ያሉ አንዳንዶችና በውጪ ያሉ አንዳንድ ቡድኖች፤ ቀን ተሌት ለውጡን አቅጣጫ ለማሳት ወይም ለማቆም እየጣሩ ነው። የዚህ የኋለኛው ክፍል ዋና መሪ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር ሲሆን፤ እሱ ያሰማራቸው ቅጥረኛ አባሪዎቹና የሱ ዓይነት አጀንዳ ያላቸው አብረው አድመዋል። የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር፤ ምንም እንኳን በመንግሥቱ አናት ላይ ባይቀመጥም፤ ቁልፍ የሆኑ ቦታዎችን በጦሩ፣ በደህንነቱና በምጣኔ ሀብት ሥምሪቱ መንግሥታዊና ከመንግሥት ውጪ በሆኑ ክፍሎች፤ አባላት አሉት። በተጨማሪም፤ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር የሀገሪቱን ሀብት መዝብሮና ጢም ያለ የመሣሪያ ክምችት ትግራይ ውስጥ ስብስቧል።

አሁን በሀገራችን ውስጥ ያለውን መንግሥት ስንመለከት፤ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ፤ እጃቸው ከኋላቸው ታስሯል። መቼም ያለ ሕግ-መንግሥትና መንግሥታዊ መዋቅሩ፤ ብቻቸውን እንዳሻቸው መንግሥትን መምራት አይችሉም። ኃላፊነቱን የሠጣቸውና ወካያቸው፤ ኢሕአዴግ ነው። የሚገዙት በኢሕአዴግ ሕገ-መንግሥት ነው። የሚንቀሳቀሱት፤ መንግሥታዊ መዋቅሩ ውስጥ ቁልፍ በሆኑ ቦታዎች ላይ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር ባስቀመጠላቸው የጦሩ፣ የደህንነቱና የየክፍሎቹ ኃላፊዎች ነው። በተጨማሪም አብረው የሚሠሩት የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር መርጦ ባስቀመጣቸው አባላት ከተሞላው ፓርላማ ጋር ነው። በሌላ በኩል፤ ጉልበታቸው፤ ለውጡና የሚወዳቸው ሕዝብ ነው። ይህ አጣብቂኝ ሁኔታ፤ የግድ ኦሕዴድ የሚመርቅላቸውን ሰዎች በየቦታው እንዲመድቡ አስገድዷቸዋል።  ኦሕዴድ ደግሞ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድና የኦሮሚያ ፕሬዘዳንት አቶ ለማ መገርሳ የሚመሩት አንድ ወጥ ድርጅት አይደለም። በዚህም ምክንያት፤ በየከተማው ሰልፉን በሚያካሂደውና ለውጡ ፈላጊው ሕዝብና ለውጡን በሚመሩት የመንግሥቱ ክፍል መካከል ክፍተት ተፈጥሯል። ለምሳሌ፤ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር በሰንደቅ ዓላማችን ላይ ያስቀመጠውን ምልክት ጥለው፤ አረንጓዴ፣ ብጫና፣ ቀይ ቀለማት ብቻ ያሉትን የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ፤ ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ድረስ፤ ሕዝቡ እያውለበለበ፤ “ተደምሬያለሁ!” እያለ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይን ስም እያሞገሰ ወጥቷል። ነገር ግን፤ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባርን ሰንደቅ ዓላማ ለማስከበር፤ መንግሥታዊ መዋቅሩ፤ እኒህን አውለብላቢዎች እያሰረ ነው። ሕዝቡ ቀድሞ፤ “አንለያይም!” “አንድ ነን!” “በዘር አጥር መከፋፈሉ ያብቃ!” “ኢትዮጵያዊ ነን!” እያለ ነው። አሁንም በየክልሉ ያሉትን መሪዎች ይሄ የሚጋፋቸው ሆኗል።

ከዚህ ላይ ግልጥ የሆነው ነገር፤ የተለየ አጀንዳ ያላቸው ክፍሎች፤ በፌዴራል መንግሥት ውስጥ ጭፍሮቻቸውን ሰግስገው በማስገባት፤ ምናልባትም በትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር እርዳታ፤ ለውጡን ለማደናቀፍ እየሠሩ መሆናቸው ነው። ይህ ደግሞ ባደባባይ የዋለው፤ የዐማራ ወጣቶችንና የኦሮሞ ወጣቶችን ለማጣላት፤ የሌለ አጀንዳ በማራገብና በመካከላቸው ክፍተት በመፍጠር ነው። ባሁኑ ሰዓት ሀገራችን ማተኮር ያለባት፤ ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚደረገውን ጉዞ ማፋጠን ነው። ሁላችንም እንደምናውቀው፤ የክልል አስተዳደሩ የተዋቀረው፤ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባርን አጀንዳ ለማራመድ እንጂ፤ ሌሎችን ማንኛቸውንም ለማስደሰት አይደለም። የክልል መስመሮቹ ማንንም አላረኩም! ትክክል አይደሉም። ምክንያቱም ትክክል የሚባል የክልል ወሰን የለማ! ዐማራው በመላ ኢትዮጵያ ይገኛል። ኦሮሞው በመላ ኢትዮጵያ ይገኛል። ጉራጌውም ሌላውም። የትኛውም ቦታ ቢሆን በተለይ ለአንዱ ወገን ተብሎ ሊከለልና ሊሠጥ አይችልም። እያንዳንዷ ኢትዮጵያዊትና እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የራሷ እና የራሱ የሆነ ንብረት፤ በየሚገኙበት ቦታ አላቸው። ሀገሪቱን ደግሞ በአንድነት ከቀድሞዎቹ ወርሰናታል። ቀጥለን ደግሞ ለመጪዎቹ እናወሳታለን። አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ናት። ትናንት የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ስሟ በረራ ነበር። ዛሬ አዲስ አበባ ተብላ ተጠርታለች። ታሪኩን ለተመራማሪዎች በመተው፤ እኔ  እማራለሁ። ባሁኑ ሰዓት፤ የአዲስ አበባ አስተዳደር፤ በአዲስ አበባ ለሚኖረው ሕዝብ መተው አለበት! ለሐረርም እንዲሁ! የአካባቢውን አስተዳደር የአካባቢው ሕዝብ መምረጥና መመደብ ይኖርበታል።

በሌላ በኩል፤ ኦሮሞዎች ከሶማሌ ክልል መባረራቸውና መገደላቸው ትክክል አይደለም። ዐማራዎችም እንዲሁ። ጋሞዎችም በቡራዮ የተፈጸመባቸው ግፍ ትክክል አይደለም። ጉራ ፈርዳ፣ ሐረር፣ አርሲ፣ ወለጋ፣ ቤንሻንጉል፣ ወልቃይት፣ ጠለምት፣ ራያ በዐማራው ላይ የተፈጸመው በደል፤ ግድያው፣ መፈናቀሉ፣ መባረሩ፣ ሀብታቸው መዘረፉ፣ ትክክል አይደለም። ባጠቃላይ በትውልድ ሐረግ የተመሠረተ ማንኛውም አጀንዳ፤ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር አጀንዳ እንጂ፤ የኢትዮጵያዊያን አጀንዳ አይደለም። ይሄን አጀንዳ አንግበው በሕዝቡ መካከል ጠብ የሚጭሩ፤ ፀረ-ሕዝብ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባርና አባሪዎቹ ናቸው።

በሕዝቡ መካከል የሚፈጠር የጎሳ ግጭት፤ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር ቅንብር ነው። ይሄም ሕዝቡ በአንድነት እንዳይቆም የሚያደርግ መርዛማ ሴራ ነው። ይሄን በማድረግ ብቻ ነው፣ አናሳው ክፍል ብዙኀኑን ሊገዛ የሚችለው። ይህ የዐማራው ወይንም የኦሮሞው አጀንዳ አይደለም። ይህ ደግሞ ለመላ ሰማንያ ሁለት ጎሳዎች የሚሠራ ነው። ቅመ አያቶቻን እና ቅድመ አያቶቻችን፤ አያቶቻችን እና ወላጆቻችን፤ ባጽምና በደማቸው የገነቧትን ሀገራችንን፤ በአንድነት ኢትዮጵያዊ ሆነን እንኖርባታለን። ያለን ምርጫ ያ ብቻ ነው። ይህ አብሮ ያሠረን ዜግነታችን ነው። አሁን በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ፣ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮነን፣ በኦሮሚያ ፕሬዘዳንት ለማ መገርሳና በዐማራ ፕሬዘዳንት ገዱ አንዳርጋቸው የሚመራውን የለውጥ ሂደት የምንደግፍ በሙሉ፤ የአንድነቱን አጀንዳ አንግበን፤ ከለውጡ ጋር መራመድና ለውጡ እንዳይስተጓጎል ዘብ መቆም አለብን። አዎ! ጉድለቶች ይኖራሉ። ነገር ግን መገንዘብ ያለብን፤ አሁን በሽግግር ላይ ነን። እኔም ቢሆን፤ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር ነቀርሳ ዛሬውኑ ከሥሩ ተመንግሎ ቢወገድ ደስ ይለኛል። ይህ ግን ምኞት ነው። ተጨባጭ ሀቅ ደግሞ ለእውነት እንድገዛ ያደርገኛል። ለፍላጎታችን ቅደም ተከተል ማበጀት አለብንና ሀገራችን እናስቀድም። የግለሰብና የቡድን አጀንዳችንን ወደኋላ በማለት፤ ሀገራችን እና የአንድነት ሰንደቃችንን በማሰቀደም፤ ወደፊት መሄድ አለብን።

የለውጡን ሂደት እደግፋለሁ፣ አንድነትን እወዳለሁ ብሎ፤ አዲስ አበባ የኦሮሞዎች ናት ማለት አይቻልም! ቀድሞ ነገር ይህ ምን ማለት ነው? ሁመራ የኦሮሞው አይደለችም? ጂጂጋስ? መቀሌስ? ይህ ያስተወሰኝ፤ ጭራቁ ሟች የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር መሪ፤ “አክሱም ለወላይታው ምኑ ናጥ?” ሲል ያላገጠበት ንግግር ነው። አሁን የሰፈሩት የትግሬዎቹ እንጂ፤ የቀሪዎቹ ኢትዮጵያዊያን አይደለም ሲለን! ይህ የክልል አስተዳደሩ ጋር መጥፋት ያለበት ጉዳይ ነው። ለአሁኑ፤ ከላይ እንዳሰፈርኩት፤ አዲስ አበባ ከክልሎቹ አንዷ በመሆኗ፤ የክልሏ ነዋሪዎች ናቸው አስተዳደሯን የመርጡትና የሚያካሂዱት። ጠባብ ብሔርተኝነት የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር እና ያራገበውና አሁን ከሱ ጋር የቆሙ የሚያራምዱት አጀንዳ ነው። የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር ዐማራውን ለማጥፋት፤ በዘር ላይ የተመሠረተ የዘር ማጽዳት በዐማራው ላይ አካሂዷል። ይሄንን ማንኛውም ዐማራ ከአእምሮው አያወጣውም። አሁን ደግሞ አምስት የኦነግ አካሎችን የሚወክልና ኢትዮጵያዊያንን በኢትዮጵያ አብረን እንድንኖር የማያስችል ንግግር፤ ከአቶ በቀለ ገርባ ሰምቻለሁ። ይህ በጣም አደገኛ ነው።

በጎንደር የተሰለፉት የዐማራ ወጣቶች፤ አቶ በቀለ ገርባን በትከሻቸው ጭነው፤ የራሳቸው መሪ አድርገው፤ “የኦሮሞዎች ደም የኛ ደም ነው!” “የእስልምና ተከታይ ወገኖቻችን ጉዳይ የኛም ነው!” “በቀለ ገርባ መሪያችን ነው!” ብለው ሲጮኹ፤ ኢትዮጵያ በወቅቱ የምትፈልገውን የመዳኛ ገመድ ፈተሉ። አቶ በቀለ ገርባ፤ “እኔ ጎንደሬ ነኝ!” “እኔ ዐማራ ነኝ!” “አመሰግናችኋለሁ!” ማለት ነበረባቸው። ይሄንን አላደረጉም። እኒያ ኩሩ ጎንደር ያሉ የዐማራ ወጣቶች፤ በአቶ በቀለ ገርባ ላይ ምንም ዓይነት ቅሬታ የላቸውም። ያን ያደረጉት ከኦሮሞ ወገናቸው ጋር አብረው በመቆም፤ “ኦሮሞ ወጣቶች መሪያችን ያሉት የኔም መሪ ነው!” ብለው ኢትዮጵያን ለማዳን ነበር። ይህ ነው ኢትዮጵያዊነት። ይህ ነው ከትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር የጸዳ ኢትዮጵያዊነት። “አዲስ አበባ የኦሮሞዎች ናት!” በማለት፤ አቶ በቀለ ገርባ በጎንደር የተሰለፉትን የዐማራ ወጣቶች በጣም አሳዝነዋቸዋል። ጥረታቸውንም ዋጋ አሣጥተውታል።

አዎ! በዘር ላይ የተመሠረተው ፌዴራሊዝም ይወድማል። አዎ! በዚህ አጀንዳ በደል የፈጸሙ፤ የትም ይገኙ፣ ከየትም ይምጡ፤ ለፍርድ ይቀርባሉ። አዎ! እያንዳንዳችን ኢትዮጵያዊያን፤ በየትኛውም የሀገራችን ክፍል፤ የመኖር፤ ሀብት የማፍራት፤ በቦታው የኅብረተሰብ ክንውን ሙሉ ተሳትፎ የማድረግ መብታችን ይከበራል። ይህ ነው ለውጡ እየገሰገሰበት ያለው ግብ።

መወያየት ለሚፈልጉ፤ eske.meche@yahoo.com

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

የሽግግር መንግሥት ማቋቋሙ፤ ግዴታ ነው።

የሽግግር መንግሥት ማቋቋሙ፤ ግዴታ ነው።
አንዱዓለም ተፈራ
ሐሙስ፣ ሐምሌ ፲ ፪ ቀን ፳ ፻ ፲ ዓመተ ምህረት

የተራበች እናት ምግብ ማግኘቷ፤ ምርጫ ሳይሆን ግዴታ ነው።
ምርጫ የሚሆነው ሰጪና ነሺ ካለ፤ ለዚሁ አካል ብቻ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ መሐመድ የኦሕዴድ መሪ ናቸው። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ መሐመድ የኢሕአዴግ ወኪል ናቸው። አሁን ኢትዮጵያን እያስተዳደሩ ያሉት፤ በኢሕአዴግ መዋቅርና ሰዎች ነው። በርግጥ የያዙት መንገድ፤ እስከዛሬ በትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር ገዥዎቻችን ሲመራ የነበረው ኢሕአዴግ ሲከተለው ከነበረው ለየት ያለ ነው። አሁንም መሠረቱ ግን ኢሕአዴግና ኢሕአዴግ ሲመራበት የነበረው የፖለቲካ ፍልስፍናና የአስተዳደር መመሪያ ነው። እናም አንድን ወገን ብቻ ወክለው፣ ነገር ግን በጣም ጥሩ ነገር ለብዙኀን በማድረግ ላይ ያሉ ናቸው። ይህ በጎ ተግባራቸው፤ ከመጡበት አኳያ ስናየው ውስንነት አለበት። በአንድ ሰው ቅንነት ሀገር አትመራም። የሚቀጥለው ምንድን ነው? ብለን ከመጠበቅ በላይ፤ ምን መሆን አለበት የሚለውን ሁላችን በያለንበት መነጋገር አለብን። የሀገራችን ችግር ምስቅልቅል ነው። ይህች ሀገር የሁላችን ናት። ለውጡን ተባብረን ቀጣይነቱን ለማረጋገጥ፤ ሁላችን መታቀፍ አለብን።

የሀገራችን ችግር ምስቅልቅል ነው። በቀጥታ አንድና አንድን እንደመደመር ሊወሰድ የሚችል አይደለም። ይሄ ምስቅልቅል ችግር፤ መሠረታዊ የሆነ ከሥሩ መንግሎ የሚጥል መፍትሔ ካልተገኘለት፤ እምቧለሌ ዙሪያ የሚሽከረከርና የማይለቅ ይሆናል። የክልል ጉዳይ አንድ ነው። ከዚሁ ጋር ተያይዞ፤ አከላለሉ፣ አስተዳደሩ፣ “እኛ” እና “ሌሎች” የሚለው ግንዛቤ፣ ርስ በርስ ሕዝቡ እንዲጋደል የተደረገው ሂደት፣ የመፈናቀልና በግፍ የመገደል ጉዳይ ሌላው ነው። አድልዖ፣ ሙስና፣ የመንግሥት ሥልጣንና የተዋረዱ ሂደት ሌላው ጉዳይ ነው። የመንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ የመግባት ሁኔታ፤ ሌላው ጉዳይ ነው። በገፍ ከሀገራቸው የተሰደዱ ኢትዮጵያዊያን ጉዳይ ሌላው ነው። አንዱን አካባቢ ከሌላው አስበልጦ የማሳደግና ዕድሉን ሁሉ በዚያ መንዳት ሌላው ጉዳይ ነው። ብዙ ከዚህ የከፉ ሌሎች ሊዘረዘሩ የሚችሉ እንዳሉ ሁላችን እናውቃለን። የሚከተለው ምንድን ይሆን? ብለን ከመጠበቅ በላይ፤ ምን መከተል አለበት የሚለውን መነጋገር አለብን።

ይህች ሀገር የሁላችን ናት። እናም ሁላችን የኔ ብለን መፍትሔ ማምጣቱ ላይ መረባረብ አለብን። ግዴታውን ለአንድ ግለሰብ ወይንም ክፍል ሠጥተን፤ ሌሎቻችን እጆቻችንን አጣጥፈን መቀመጥ የለብንም። ባለፈው ግማሽ ምዕተ ዓመት በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የደረሰው ጥፋት፤ በኢትዮጵያዊያን የተፈጸመ በመሆኑ፤ የኛው ታሪክ ነው። እናም አብሮን ለምጥ ሆኖ ለዘለዓለሙ ይኖራል። አሁን እንዲቀጥል የምንፈቅድበት ወይንም በትብብር እንዲቆም የምናደርግበት ዕድል ገጥሞናል። ኋላ ዞረን ያኔ እንዲህ ቢደረግ ኖሮ! ወይንም እኔ እንዲያ ባደርግ ኖሮ! ብለን የመቆጫው ጊዜ፤ ሊመጣ አይገባውም። አሁን ማድረግ ያለብንን፤ አሁን ማድረግ አለብን። እናም ትክክለኛው ጥያቄ፤ የሽግግር መንግሥት ይቋቋም ነው።

የሽግግር መንግሥትን መቋቋም የማይፈልጉ አሉ። እኒህ በሁለት ይከፈላሉ። የመጀመሪያዎቹ፤ አሁን ያለውን የለውጥ ሂደት ስለሚጠሉት፤ እንዲከሽፍና የነበሩበት መንበር እንዲመለስላቸው የሚደክሙት ናቸው። ሌሎቹ ደግሞ፤ የተጀመረው ለውጥ እንዲቀጥል ስለሚፈልጉና ለውጡ ይነጋነጋል ብለው ስለሚፈሩ፤ ሁሉን ነገር ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እንተውላቸው ባዮች ናቸው። የመጀመሪያዎቹን መነጋገር ያለብን አይመስለኝም። እናም አልፈዋለሁ። ሁለተኛዎቹን በሚመለከት፤ ያንድ ሰው ድካም ይበቃል ወይንስ ሁላችን የምንረባረብበት? በሚል እመልሰዋለሁ።

አንድ ብቻቸውን የሚደክሙት ጠቅላይ ሚኒስትር፤ ባሁኑ ጊዜ፤ ዙሪያቸውን ከከበቡት መካከል ነባር የሕዝቡ ጠላቶች አሉ። በግለሰብ ደረጃ እሳቸውን፤ ያን ካልቻሉ ደግሞ ሥራቸውን ለማደናቀፍ ወደኋላ የማይል ኃይል አለ ማለት ነው። መርሳት የሌለብን፤ ሕይወታቸውን ለማጥፋት ሞክረዋል። እሳቸውን ማጣት ከባድ ውድቀት ነው። ነገር ግን፤ በሳቸው ተማምኖ መጋለብ ኃላፊነት የጎደለው ሂደት ነው። እሳቸውን መንገር ያለብን፤ አሁን ሀገራችን የምትፈልገው፤ የሽግግር መንግሥት ተቋቁሞ፤ ውስብስቡን የሀገራችን ችግር፤ ባገር አቀፍ ጥሪ መፍታት ነው። እንዴት ሊቋቋም ይችላል? እንዲህ አይሆንም ወይ? ያ ችግር አያስኬድም? የመሳሰሉ ምክያቶችን መደርደር ይቻላል። ነገር ግን ከዚህ የቀለለ ሌላ መንገድ የለም። ስለ ሽግግር መንግሥት አቋቋም፤ በሚቀጥለው ጽሑፌ በሠፊው እሄድበታለሁ። ወይንም ሌሎች ሊያቀርቡ ይችላሉ። ዋናው ግን፤ ካለንበት አዘቅት መውጣት የምንችለው፤ ካሁኑ ቦታችን ወደምንፈልገው ቦታ ለመድረስ፤ የሽግግር መንግሥት ግዴታ ነው። ምን ትላላችሁ?

ከታላቅ አክብሮት ጋር
አንዱዓለም ተፈራ

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

ደርሶ መልስ

ደርሶ መልስ 

( ክፍል ፩ )

አንዱዓለም ተፈራ
የካቲት ፱ ቀን ፳ ፻ ፲ ፪ ዓመተ ምህረት  ( 2/17/2020 )

ኢትዮጵያ ሀገሬ ደርሼ ከመጣሁ ሶስት ቀን ሆነኝ። ልቤ ውስጥ ተሰንቅሮ የተቀመጠ ጉዳይ አላስተኛኝ ስላለ፤ ይሄን መጻፍ ጀመርኩ። የምጽፈው ለማንም ሳይሆን ለራሴ ነው። መጻፉን የወደድኩት፤ ከጭንቅላቴ ወጥቶ በፊቴ ላይ ሳየው ቀለል ይለኛል በማለት ነው። በርግጥ ከራሴ አልፎ በድረገጽ ላይ ስላሳረፍኩት፤ የግሌ ብዬ ማለቱ ችግር ነው። ለገር ግን በድረገጽ ላይ የሰፈረው በኔው መናዘዣ የእስከመቼ መድረኬ ላይ ስለሆነ፤ አሁንም የራሴ ከመሆን አያልፍም። ይሄን የእስከመቼ የድረገጽ መድረኬን ከጫርኩበት ብዙ ጊዜ ሆኖኛል። እናም እጅግ በጣም ጥቂት የሆኑ ጎብኝዎቼ፤ ለረጅም ጊዜ እንዳልዳሰስኩት ሲገነዘቡ፤ መጥተው ማየታቸውን ትተውታል! ብዬ ወስጃለሁ። አሁን ወደ ጽሑፌ ልመለስ።

በስደት ላይ ከመሆኔ በፊትም ሆነ በኋላ፤ ለስደት ያበቃኝን ምክንያት ትቼው አርፌ አልተቀመጥኩም። ዛሬ ከረጅም ጊዜ በኋላ ደርሼ ስመለስ፤ ጥልቅ ግንዛቤ አደረግሁ። በርግጥ ምን ጊዜም ቢሆን ኢትዮጵያዊነቴ ከኔ ሊወጣ አይችልም። ይህ ምን ጊዜም አብሮኝ የሚኖር ሀቅ ነው። ደርሶ መልሴ፤ ምንነቴን፣ የሕይወቴን ጉዞ፣ የቤተሰቤን ኃላፊነት፣ የኔን የፖለቲካ ተሳትፎና ውጤት፣ ከሌሎች ኢትዮጵያዊያን ጋር ያለኝን ግንኙነት፣ የወደፊቴን እንድመረምረው አደረገኝ። ለዚህ ሁሉ መሠረቱ በሀገራችን ውስጥ ያለው ሀቅ ነው። እንዴት ተረዳሁት? ምን ሁኔታ አለ? ወደየት እየተሄደ ነው? ምን ሊከተል ይችላል? ይህ እንዲሆን ነበር ወይ ያለፉትን የሕይወቴ ሃምሳ ዓመታት በትግል ስንገላታ ያሳለፍኩት? ሕይወታቸውን በሂደቱ ያጡ ጓደኞቼስ ትርክት ምን ሊሆን ነው? ይህ ነው የዚህ ጽሑፌ ትኩረት። በዚህ በመጀመሪያው ክፍል፤ ላይ ላዩን የተመለከትኩትን እዘክራለሁ። በተከታታዮቹ ደግሞ፤ ጥልቁንና ወደፊት የሚለውን አሰፍራለሁ።

አብዛኛውን ጊዜዬን ያሳለፍኩት ጎንደርና አዘዞ ነው። አዲስ አበባ ቆይቻለሁ። ባሕርዳርን ጎብኝቻለሁ። መራይን ውየባታለሁ። አዲስ አበባ ሉሲን እንደ የውጪ ሀገር ጎብኚ ሆኜ ዓይቻታለሁ። የቀይ ሽብር ሰለባዎች መታሰቢያውን ጎብኝቻለሁ። ጎንደር አስደናቂውን የሁለት ሺ አስራ ሁለት ዓመተ ምህረት የጥምቀት በዓል ታድሜበታለሁ። ሰዎች መደርደሪያው ተንዶ ጉዳት ሲደርስባቸው እዚያ ነበርኩ። አዘዞም የሎዛ ማርያም አስተሮዬን በዓል አክብሬያለሁ። አስቤ የነበረውን የሀገሬን ታሪካዊ ቦታዎች መጎብኘት ሳላሳካው ተመልሻለሁ። ከዚያ በተረፈ ግን፤ በጣም ጥቂት የሆኑ በሕይወት ያሉ የሚያውቁኝና የማውቃቸውን አዲስ አበባና ጎንደር አግኝቼ፤ አብሬያቸው የድሮውን ስዘከር፣ ስበላና ስጠጣ፣ ከሕዝቡ ጋር በየመንገዱና በየታክሲው ስተራመስ ከርሜያለሁ። ይሄው ከሕዝቡ ጋር ስተራመስ የሰነበትኩበት የላይ ላይ ዕይታ እነሆ!

ዕድሉን አግኝቼ ሀገሬ ገብቼ፤ በቀብር ስነሥርዓቷ ላይ ልገኝ ያልቻልኩትን እናቴን፤ ከብዙ ጊዜ በኋላ የመቃብር ቤቷ ሄጄ፤ በተደጋጋሚ አነጋገርኩና ተሰናበትኳት። ይሄን በመታደሌ ደስታ ተሰምቶኛል። አጠቃላይ ደርሶ መልሴ የተደባለቀ ስሜት አሳድሮብኛል። ሀገርን ተገዶ አርባ ዓመት የሚጠጋ እንዳይመልስ የተደረገ ሰው፤ በሚመለስበት ወቅት የሚጠብቀውን አያውቀውም። እኔም ስመለስ ምን ሊሰማኝ እንደሚችል ቀርቶ፤ ምን እንዲሚገጥመኝ በትክክል አላውቀውም ነበር። እናም ይቅር አዲስ አበባና ጎንደር፣ ተወልጄ ላደግሁባት አዘዞ እንኳ፤ እኔ ለሷ፣ እሷ ለኔ አዲስ ነበርን። በጣት የሚቆጠሩ ብቻ ነበሩ ያወቁኝና ያወቅኋቸው። እንግዲህ በዚህ ተጀምሮ የት ሊደረስ እንደሆነ መገመቱ አይቸግርም!

አንዳንድ የታዘብኳቸው ነገሮች አሉ። የማውቀውን የአዲስ አበባ ፒያሳ፣ ከማዘጋጃ ቤቱ ተነስቼ በሲኒማ ኢትዮጵያ አልፌ፣ በግሬ እስከ አራት ኪሎ ድረስ፤ ገና ደርግ ደርግ ነኝ ብሎ ሳይወጣ እንደተውኩት አገኘሁት። በተመሳሳይ መልኩ የጎንደር ፒያሳም እንዲያ ነበር። በሌላ በኩል የየከተማዎች ነዋሪ ሰው ቁጥር ከመጣን በላይ አድጓል። ቁጥሩን የሚያውቅ ሰው አለ ብዬ አልገምትም። አዲስ አበባም! ጎንደርም! አዘዞም! ከተማዎቹ ተለጥጠው፣ ተለጥጠው፣ ተለጥጠው፤ ካንዱ ጫፍ ወደሌላው ጫፍ ለመድረስ፤ ሌላ ሀገር የመሄድ ያህል ሆኗል። የመኪናው ቁጥር እጅግ በዝቷል። መንገዶቹ ጠበዋል፣ በዝተዋል፣ አስፋልትና የኮብል ንጣፍ በየቦታው ተደቅድቋል። ይሄ ሁሉ ሆኖ፤ የመኪናዎቹ ቁጥር፤ የሕዝቡን የመጓጓዝ ፍላጎት ያሟሉ አልመሰለኝም። ይሄን ልል የቻልኩት፤ በየታክሲዎች ማቆሚያ ላይ ያየሁት እጅግ ቁጥሩ የበዛ የሕዝብ ሰልፍ ነው። ባጃጅ እንዳፈር መሬቷን ሞልቷታል። ከተማዎችም ሆኑ የገጠር አካባቢዎች፤ ባጃጅ ያልገባባቸው አላየሁም። በዚህ ሁሉ ልክ፤ በየከተማዎቹ የመጸዳጃ ቦታዎች በየቦታው አለመኖራቸው፤ እንደልብ መንቀሳቀስ ለአፍንጫ አስቸጋሪ ነበር። አንዳንድ ቦታማ መረገጫ ቦታ እንኳን አሳጥተውኛል። ሰዎችን ያለቦታው ሲከፍሉ ማየት፤ “ድሮኮ ነውር ነበር!” አስብሎኛል። በየከተማው ያየሁት የሆቴሎች፣ የምግብ ቤቶች፣ የቡና መጠጫ ስፍራዎች ብዛት፤ ዓይኖቼን አፍጥጬ መዝጋት እስኪሳነኝ አስገርሞኛል። “እውነት እኒህ ሱቆች በሙሉ ለባለቤቶች በልቶ ማደሪያ ትርፍ ያስገኛሉ?” ይሄን ደጋግሜ ለራሴ ጠይቄያለሁ! መልስ እንዳላገኝ፤ የጠየቅሁት አዋቂ አልነበረም። በየቦታው ያየኋቸው የፎቆች ጋጋታ፤ ከግራሞት በላይ ነበሩ። ግዝፈታቸው! መለያየታቸውና ቁንጅናቸው! አፍ ያስከፍታል። አዲስ አበባ መገናኛ፤ አንድ የገበያ አዳራሽ ገባሁና፤ የፎቅ መውጫ ተንቀሳቃሽ ደረጃውን፣ በየሱቆቹ ያሉትን ልብሶችና የቤት ዕቃዎች ተመልክቼ፤ እውነት አዲስ አበባ ነው ያለሁት! በማለት ዙሪያዬን አገላብጬ አትኩሬ ፈትሻለሁ።

ከቻይና የምዕራባዊያን ዕቃዎች በቅጅ ተገልብጠው፤ የበለጠ አምረው ጥራታቸው ግን ወደታች ወርዶ በየቦታው ዓይቻለሁ። ገዥና ዋጋ ይፈራረሙበት! ብያለሁ። ለነገሩ ምን የምዕራባዊያን ዕቃዎች ብቻ! የኛው የጅ ሥራም አልቀረለት! የሴቶች የፈትል ቀሚስ በቻይናዎቹ ቀጂዎች ከነጥለቱ ተኮርጆ፤ በየሱቁ ተደርድሮ ሳየው፤ “ወየሁ ጉድ! ፈታይ፣ ሸማኔና ጠላፊ ሥራ ፈት ሊሆንና፤ ብር ወደ ቻይና! ረሃብ ወዳገሬ!” አሰኝቶኛል። ለሺያጭ የተደረደሩትን ዕቃዎች በሙሉ ስመለከት፤ የት ነው ያለሁት? ብዬ እንድጠይቅ ደጋግሞ ነካክቶኛል። ቀድሞ የነበርኩበትና የአሁኑ አለመዛመዳቸው ብቻ ሳይሆን፤ ፍጹም የማይገናኙ መሆናቸው፤ አእምሮዬን በጥርጣሬ ስለሞላው፤ የትኛው ነው እውነት? ብዬ እንድጠይቅ ተገድጃለሁ! መቼም በሃያኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያና በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ መካከል ያለውን የመቶ ዓመታት ክፍተት፤ ባንድ እመርታ ዘሎ መግጠም አይቻልም!

ከከተማዎች ሲወጡ፤ ከሞላ ጎደል የገጠሩ ሰው አለባበስ ተለውጧል። የማውቀው የአርሶ አደር ልብስ እየጠፋ ሄዷል። ይሄ ለበጎ ነው፤ ለሥራ የሚያመችና የጸዳ ልብስ ማየት ደስ ያሰኛል። በተለይ ደግሞ፤ በአርሶ አደሩ ዘንድ ገንዘብ እንዲያ ደርቶ ሲንሸራሸር ማየቴ አዲስ ሆኖብኛል። የማልክደው ደግሞ፤ በልመና የተሰማራው ሰው ቁጥር እጅግ በዝቶ አግኝቸዋለሁ። ምንም እንኳን በትክክል ወይንም ትክክለኛ ባልሆነ መንገድ በልመና የተሰማሩ አሉ! የሚለውን በግንዝቤዬ ውስጥ ባስቀምጥም፤ በውል ቁጥሩ ራሱ አስደንግጦኛል። በተለይም ሕጻናትን የያዙ፣ አካላቸው በአውነት የጎደለና አዛውንቶችን ሳይ በጣም ተሳቅቄያለሁ። እንግዲህ ይሄ ሁሉ የሚታየው እውነታ ነው። ከሚታየው ጀርባ ያለው፤ ይሄን ሁሉ አንቀሳቃሹ የፖለቲካው፣ የኢኮኖሚውና የባሕሉ ሀቅ፤ ጭንቅላት ያሳክካል። ያን በሚቀጥሉት ተከታታይ ክፍሎች አቀርባለሁ።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | 2 Comments

አፍሪካና የወደፊቷ! በስታንፈርድ ዩኒቨርሲቲ የሁቨር ኢንስቲቱት መድረክ

አፍሪካና የወደፊቷ! በስታንፈርድ ዩኒቨርሲቲ የሁቨር ኢንስቲቱት መድረክ
ማክሰኞ፣ ጥር ፯ ቀን፣ ፳ ፻ ፲ ፩ ዓመተ ምህረት፤ (1/15/2018)

“የወደፊቱ ክፍት ነው። ገና ምንነቱ አልተረጋገጠም።”
ተናጋሪውን ገና ያላወቅሁት

በዩናይትድ ስቴትስ ኦቭ አሜሪካ፤ የአስተዳደር መመሪያዎች የሚመነጩት፤ አብዛኛው ሕዝብ ይወደዋልና ይደግፈዋል ከሚል ግንዛቤ ተነስተው ነው። ለዚህ እንዲረዳ፤ የጉዳዩ አቀንቃኞች፤ ሕዝቡን ለማግባባት፤ በየቦታውና በየጊዜው መድረኮችን ፈጥረው ምሁራንን በመጋበዝ፤ በርዕሱ ዙሪያ፤ የሚፈልጉትን በማስቀደም፤ ለታዳሚዎቹ ተደጋጋሚ ገለጣዎች ያደርጋሉ። ከነዚህ መድረክ አዘጋጆች አንዱ ካሊፎርኒያ በሚገኘው ስታንፈርድ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ያለው የሁቨር ኢንስቲቱት ነው። በዚህ ኢንስቲቱት ውስጥ፤ ከፍተኛ የቀድሞና የወደፊት የፌዴራሉ መንግሥት ኃላፊዎች ተሰግስገው ይገኙበታል። ባሁኑ ሰዓት፤ ቀድም ሲል በነበሩት የሬፓብሊክ ፓርቲ ፕሬዘዳንቶች ወቅት የስቴት ዲፓርትመንት ጸሐፊ የነበሩት ጆርጅ ሹልትዝ እና ኮንዶሊዛ ራይስ ከሌሎች ዕውቅ ምሁራንና አኳያዎቻቸው ጋር ይገኛሉ።

ጆርጅ ሹልትዝ “በታዳጊው ዓለም ክፍል፤ የአስተዳደር ጉዳይ” የሚል ተከታታይ መድረኮችን የሚያቀርብ ዝግጅት አላቸው። ትናንት ሰኞ፣ ጥር ፮ ቀን፣ ፳ ፻ ፲ ፩ ዓመተ ምህረት፤ (1/14/2018) በዚሁ በስታንፈርድ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ፤ “አፍሪካ፤ በታዳጊው ዓለም ክፍል፤ የአስተዳደር ጉዳይ” በሚል ርዕስ፤ ራሳቸው ጆርጅ ሹልትዝ በተገኙበት፤ ከሰዓት በኋላ፤ ከምሽቱ ፲ ሰዓት እስከ ፲ ፩ ከሩብ ድረስ፤ መድረክ አዘጋጅቶ ነበር። ማስታወሻና ግንዛቤዬ እነሆ!
stanford hoover discussionፎቶግራፉን የወሰድኩት ከዝግጅቱ ድረገጽ ላይ ነው።

በመድረኩ ላይ እነማን ተገኙ?

ለሕዝብ ክፍት ሆኖ በጆርጅ ሹልትዝ በተከፈተው ውይይት፤ በአስተዳደር፣ በቴክኖሎጅ፣ በንግድ፣ በአየር ጠባይ የለውጥ ሂደት፣ በእርሻ፣ በተቋማት ምንነትና ጥቅም፣ በአፍሪካ ፖለቲካና ዕድገት፣ በተለያዩ ወገኖች መካከልና በርስ በርስ ባሉ ግጭቶች ጠለቅ ያለ ዕውቀት ያላቸው የዩኒቨርሲቲ ልሂቃንና የቀድሞ የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣን ነበሩ።

በዕለቱ የተሳተፉት፤ አንቶኒ ኬሮል ከማንቸስተር ንግድ ድርጅት፣ አምባሳደር ቸስተር ክሮከር ከጆርጅታውን ዩኒቨርሲቲና በአሜርካ መንግሥት የቀድሞ የአፍሪካ ጉድዮች ረዳት የስቴት ጸሐፊ፣ ማርክ ጅዎርዲኖ ከጆርጅታውን ዩኒቨርሲቲ፣ ጃክ ጎልድስቶን ከጆርጅሜሰን ዩኒቨርሲቲና አንድሬ ፒየናር ከ ሲፋይፍ ካፒታል ነበሩ። መድረኩን የመሩት ብቸኛው ጥቁሩ የጆርጅታውን መምህርና በአሜርካ መንግሥት የቀድሞ የአፍሪካ ጉድዮች ረዳት የስቴት ጸሐፊ፣ አምባሳደር ጆርጅ ሙስ ነበሩ።

የመድረኩ ዋና መወያያ ነጥብ ምን ነበር?

በኒህ ልሂቃን ግንዛቤ፤ በአፍሪካ ውስጥ የቴክኖሎጂ ግስጋሴ፣ የሕዝብ ቁጥር ዕድገትና፣ የአየር ጠባይ መለዋወጥ ወደፊት ተደማምረው የሚያመጡትን የለውጥ ሂደት መመልከት አስፈላጊ ነው። በዚህ ላይ፤ እኒህ ጉዳዮችና የለውጥ ግስጋሴያቸው፤ በአፍሪካ ውስጥ በሚገኙት ሃምሳ አራት ሀገራት የሚያስከትሉትን መመርመር አስፈላጊ ነው። በኒህ ጉዳዮች ላይ እየተከተለ ያለው ለውጥ፤ በመንግሥታቶቹና በመዋቅሮቻቸው፣ በብቃታቸውና በአስተዳደር ዝግጅታቸው፣ በተጨማሪ ደግሞ በኅብረተሰቡ ውስጥ ባሉ ሕዝባዊ ተቋማት ላይ የሚያመጣው ጫናና እኒህ ክፍሎች ግንዛቤያቸውና ሊያደርጉ የሚችሉት ምንድን ነው? የሚለውን መመለከት ነበር ጉዳዩ።

የውይይቱ ተሳታፊዎች፤ አዳማጩ እንዲገነዘብ የፈለጉት፤ በዓለም ዙሪያ ቀልጣፋ ለውጦች እየተንጎደጎዱ መሆናቸውን፤ የሕዝብ ቁጥርና የሕዝብ ብዛት መኖሪያ ቦታዎች እየተቀያየረ መሆኑን፤ የቴክኖሎጂ ዕድገት ከመቼውም በላይ እየናረ መምጣቱን ነው። እኒህ ቅይይሮች ደግሞ በሁሉም ቦታ እየተደመጡ እንደሆኑ ነው። እና እንዴት አድርገን ነው ይሄን አፍጥጦ ከፊታችን የተጋረጠ አዲስ ዓለም እንድንጋፈጠው የሚረዳን ዘዴ የምንቀምረው? የሚል ጥያቄ ለራሳቸው ደግነው፤ መልሱን ሁኔታውን በመረዳት መጀመር እንችላለን! በሚል ምሁራኑ ሃሳባቸውን አቅርበዋል።

ሁቨር ኢንስቲቱቱ ግራ ቀኙን ሲቃኘው፤ የዓለም ሕዝብ ሰፈራ ሁኔታ እየተቀያየረ ነው። ይህ ደግሞ በሁሉም ኅብረተሰቦች ዘንድ ከፈተኛ ጫናን ይፈጥራል። በሥልጣኔ ቀድመው የሄዱ ሀገራት፤ የተኪ ትውልድ ቁጥር መቀነስ ችግር እያጠቃቸው፤ የሕዝቦቻቸው የመኖር ዕድሜ ደግሞ ከፍ እያለ ነው። ለሥራ የሚሰማራው ወገን ቁጥሩ ሲመነምንና የአዛውንቱ የጡሮታና እንክብካቤ ዋጋ ሲንር፤ መንግሥታቱ ሌሎች አፍሪ መዋዕለ ንዋዮችን ማድረግ እጁ ያጥራቸዋል።

በዕለቱ የተደረገው ውይይት መድረኩ ይህ ነበር።

ያሳሰባቸው ምንድን ነው?

እንግዲህ ከላይ እንደሰፈርው፤ ምሁራኑን ያሳሰባቸው፤ በአፍሪካ የወጣቱ ቁጥር እየበረከተ፤ በቴክኖሎጅ ዕድገትና በሀብት ክምችት ግን ያን ያህል ያልዳለበ፤ መንግሥታቱ ደግሞ በቂ ዝግጅት ያላደረጉና አስፈላጊ ተቋማት በቦታው የሌሉበት መሆኑ ነው። ከነሱ ጥቅም አኳያ፤ የአፍሪካ የሕዝብ ቁጥር እየጨመረ መሄድ፤ በዚህ ቁጥር ደግሞ አብዛኛውን ቦታ የሚይዘው ወጣቱ መሆኑን፤ እንደ ዕድልም እንደ ዕርግማንም ያዩታል። ዕድል ብለው ያሉት፤ ወጣቱ መብዛቱ፣ ሠራተኛ መብዛቱ ነው። አፍሪካ በሥልጣኔ ወደፊት ስትሄድ፤ ከተማዎቹ እያደጉ፤ የገጠር ሰፈራው እየመነመነ ይሄዳል። በየከተማው የሚኖረው የወጣት ስብስብ፤ ትልቅ ጉልበት ይሆናል ማለት ነው። ይህ ወጣት የቴክኖሎጂ ከመቅጽበት ዕድገትን በቀላሉ እየተቀበለ፤ ትምህርትና ገንዘብ ካገኘ፤ በያለበት አምራች ሆኖ፤ ከአፍሪካ አልፎ ለነሱም እንደሚረዳ ያምናሉ።

በተቃራኒው ዕርግማን የሚሆነው ደግሞ፤ አይቀሬው የከተማዎች መድለብና የገጠር ነዋሪዎች እያነሱ መሄድ፤ ወጣቱን ከተማ ውስጥ እንዲከማች መሆኑ ዕውቁ ነገር ነው። ይሄን በርግጠኝነት መናገር ይቻላል። ነገር ግን፤ አሁን ያሉት የአፍሪካ መሪዎች ትክክለኛ አስተዳደር ይዘዋል ወይ? የሚለው አስግቷቸዋል። መጪዎቹንም ይጠይቃሉ። አስተዳደር ማለት፤ መምርያ አውጪ ሰዎች፣ ውሳኔ መሥጠትና አሠጣጡ፣ የውሳኔዎቹ ጥራትና ሂደቱ፣ ሕጎች፣ ደንቦች፣ ተቋማትና ባህላዊ አሠራሮች ባንድ ላይ ተደምረው ነው። እኒህ ደግሞ በሥልጣን ላይ የተቀመጠውን ክፍል ወሳኝ ያደርጋሉ።

እዚህ ላይ በሰዎች መካከል የሚደረገውን የግንኙነት መሰመር፣ የአየር ጠባዩ መለዋወጥ፣ የመዋዕለ ንዋይ ስምሪትና የቴክኖሎጅው ዕድገት ተጽዕኖ ያደርግበታል። እንዲያውም አልፎ ተርፎ ይወስነዋል ማለት ይቻላል። ለምሳሌ በሀገራችን፣ በዘላኖች መካከል የወንዝ መድረቅ ግጭት ያስከትላል። በዘላኖች መካከል ብቻ ሳይሆን፣ ባካባቢው ነዋሪ ሕዝብና በመንግሥት አካላትም ውስጥ ችግር ይፈጥራል። በአፍሪካ ባጠቃላይ፤ የቅኝ ግዛት ርዝራዥ የሆነው አሠራሩ፣ ሀብት ክምችቱ፣ የፖለቲካ ሥልጣት አወራረሱ፣ ለወደፊቱ ለሞከተለው እውነታ ተፅዕኖ አላቸው።

የትምህርት ጉዳይን አንስተው አቅርበዋል። በቅርብ ጊዜ ብዙ ከፍተኛ ተቋማት መቋቋማቸውን በማሞገስ አንስተዋል። ወደ ኢትዮጵያ ተመልክተው፤ ተቋማቱ ቢበዙም፤ የትምህርቱ ደረጃ የዘቀጠ ነው ሲሉ የነበረውን የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር መንግሥት አንኳሰዋል። ድሮም ሀገር ለመጥቀም ሳይሆን፣ ይህ ለወግ የተደረገ እንደሆነ የኢትዮጵያ ሕዝብ ቀድሞ ያውቀዋል። አንደኛው ተናጋሪ፤ ይህ የቴክኖሎጅ ዕድገት፣ የአየር ጠባይ መለዋወጥና የሕዝብ ቁጥር መጨመር ሂደት፤ በቅጡ ካልተያዘ፤ ግጭቶች እንደሚበዙ አትተዋል። ግጭቶች ደግሞ በሀገራት መካከልና በሠራዊት መካከል ብቻ ሳይሆን፣ የታጠቁ ኃይላት በያሉበት የሚያደርጉት እንደሆነ አስምረውበታል። በዚህ መልክ በተደረገ ግጭት የሚመጡ መሪዎች፤ ቅንነትና ሀገር አቀፍ አመለካከት ሳይሆን የሚኖራቸው፤ የግሌ የራሴ የሚልና ለተለየ የራሳቸው ወገን የሚሠራ መመሪያና ተግባር ነው የሚከተሉት አሉ። በእኛ ሀገር ባለፈው መንግሥት ሂደት የተከሰተውን ምሳሌ ማድረግ ይችሉ ነበር።

የዓለም አቀፍ ዕርዳታ፣ የዚህ ዕርዳታ አሠጣጥ እና ተቀባዮቹን በሚመለከት፤ ሰፋ ያለ ማብራሪያ አቅርበዋል። በመነሻ፤ አንድ የዓለም አቀፍ ኅብረተሰብ የሚባል ነገር የለም አሉ። ይልቁንም የውድድር ጥድፊያ፣ የተለያየ የጥቅም መስመር ይዞ ሩጫ፣ የተለያዩ ግፊቶች የሚደረግበት ነው፤ ሲሉ የዕርዳታውን ሂደት ገለጡት። አፍሪካን በሚመለከት፤ አንድ የዓለም አቀፍ ኅብረተሰብ የለም። የተለያዩ የውጪ ኃይላት ነው ያሉት። እኒህ ኃይላት ደግሞ፤ የየራሳቸው የሆነ የተለያየ ዕይታዎች ነው ያሏቸው። ከነዚህ ውስጥ ቅኖች ሆነው፤ አህጉሩን ለመርዳት ያሰቡ ይገኙባቸዋል። በአንጻሩ ደግሞ በተቃራኒው የቆሙ አሉ። ሁሉንም ወደዚህ የሳባቸው፤ የየራሳቸው የሆነው ፍላጎትና ይህ ፍላጎታቸው የፈጠረው ግፊት ነው።

ለኒህ ምሁራን ጥያቄዎቻቸው፤ ለመጪው አይቀሬ ለውጥ፤ የአፍሪካ መንግሥታት ምንድን ነው ዝግጅታቸውና ምንድን ነው እያደረጉ ያሉት? ከመንግሥታቱ ውጪ ያሉ የተደራጁ ክፍሎችስ በመንግሥታቱ ላይ ምን ያህል ጫና ማድረግ ይችላሉ? እያደርጉስ ናቸው ወይ? የሚሉት ናቸው።

መቼም ሳይነኩት የማያልፉት ነውና፤ የቻይናን ጉዳይ አነሱ። ባሁኑ ጊዜ ቻይና በአፍሪካ የምታደርገውን እንቅስቃሴ አትኩረው ተመለከቱ። ለኛ ደግሞ፤ ከኢትዮያ አንጻር ይህ ምንድን ማለት ነው? ብለን እንየው።ቻይና በሀገሯ ማምረት የምትችለውን የጨርቃ ጨርቅና አላቂና ተለዋዋጭ ዕቃዎች፤ ኢትዮጵያ ውስጥ እያመረተች፤ ወደ አውሮፓ ማጋዝ ይዛለች፤ በሰፊውም አቅዳለች። ይህ እንግዲህ ከሁለት አንጻር ይወሰዳል። እኒህ ውጤቶች በኛ ሀገር ሲመረቱ፤ በርካሽ የጉልበት ዋጋ ነው። አስከትሎ ደግሞ፤ በአጭር ጊዜ ወደ አውሮፓ ስለሚቀርቡ፤ ጊዜ እንዳያልፍባቸው ይሆናል። ላጭር ጊዜም ቢሆን እኛ እንጠቀማለን። የጥቅሙን ያንበሳውን ድርሻ ወሳጇ ቻይና ናት።

ባጠቃላይ ቻይና በአፍሪካ ውስጥ ስለሚካሄደው የሰብዓዊ መብቶች ረገጣና የሙስና ተግባር፤ አንዲት ቅንጣት ደንታ የላትም። ይልቁንም መሪዎቹ ለሚመዘብሩት የሀገር ሀብት ማግበስበስ ዐይኗን ትጨፍናለች። ይህ ደግሞ ወጣቱን እንዲያማር ያደርገዋል። ሀብቱ ሲመዘበርና ሀገሪቱ በትክክል ሳትመራ ስትቀር፤ ሕዝቡ ይነሳል። ይህ እኒህን ምሁራን አሳስቧቸዋል። በሂደቱ የአፍሪካ መሪዎች ሁለት ናሙናዎች አሏቸው፤ ይላሉ። አንደኛው የምዕራባዊን ተምሳሌ ይሆናል። ሌላው የቻይና ተምሳሌ ነው። እናም ከሁለቱ መምረጥ አለባቸው፤ ሲሉ አቅርበዋል። እኛ ቅኖች ነን የሚል መልዕክት አውለብልበዋል።

በጥያቄና መልሱ ወቅት፤ አንዲት ታዳሚ፤ አፍሪካ ብዙ ማዕደናት እንዳሏትና፤ ሁሉም የውጪ መንግሥታት ያን ለመመዝበር ወደኋላ እንዳላሉ በማስመር፤ የቻይናም ሆነ የምዕራባዊያን ጥቅም ፍለጋ እንዴት እንደሚካተት ጠየቀች። ይሄን ከንግድ ጉዳይ ጋር አስማምተው፤ አህጉሩ ከፍተኛ የማዕድን ክምችት እንዳለውና ይሄን በትክክል መጠቀም እንዳለበት ብቻ ጠቅሰው አለፉ። ቀደም ሲል መፍትሔውን በሚመለከት፤ በየሀገሩ በቦታው የተቀመጡ መንግሥታት ጥራት ወሳኝ ነው። ከመንግሥት አጓዳኝም ያሉ ተቋማት፤ ኃላፊነት አለባቸው። እኒህ የሚሠጧቸው ውሳኔዎች ሁሉን ነገር ይነካካሉ። የመጀመሪያ ደረጃ፣ ሁለተኛ ደረጃና ሶስተኛ ደረጃ ትምህርትና ተማሪዎች ጥራታቸው የተጠበቀ ሆኖ መገኘቱ አስፈላጊ ነው። የሀገር ውስጥና የውጪ መዋዕለ ንዋይ ባግባቡ እንዲመጣጠን መንግሥት መወሰን አለበት። በውጪ ዕርዳት ላይ ያተኮሩ መንግሥታት፤ ለራሳቸው ሕዝብ ደንታ አይኖራቸውም፤ ሲሉ ገልጠዋል።

ኢትዮጵያን በሚመለከት፤ አሁን በሥልጣን ላይ ባሉት በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ላይ ከፍተኛ ተስፋ አላቸው። የአስተዳደራቸውን ሂደት በጣም አድንቀዋል። እንዲህ ያሉ መሪዎች ሀገራቸውን ይጠቅማሉ በማለት ዘክረዋቸዋል። አፍሪካ የሃምሳ አራት ሀገራት ስብስብ መሆኗን ደጋግመው አንስተዋል። እናም ሌላው ችግር፤ የተለያዩ ሀገራት የየራሳቸው የጉዳይ ቅደም ተከተል ስለሚኖራቸው፤ ይሄ ከፍተኛ አደጋ አለው፤ ሲሉ ተችተዋል። የአፍሪካ ችግር የኛ እንዳይሆን የሚለው ስጋታቸው፤ ከመጀመሪያው እስከመጨረሻው ድረስ በግልጥ ይታይ ነበር። የሚገርመው፤ ከአፍሪካ ምጡቅ ተማሪዎችን አምጥተን እዚህ እኛ ማስተማር አለብን። ለዚህም የአፍሪካ ሰዎች ወደ ሀገራችን እንዲገቡ የምናደርገውን አቀባበል ማስተካከል አለብን፤ በማለት አቅርበዋል። እዚህ ተምሮ፣ እዚ ቆይቶ፤ ወደ አፍሪካ የሚመለሰውን፤ ታሪክ ይታዘበው።

እዚህ ላይ መገለጥ ያለበት ጉዳይ አለ። ይህ ውይይት፤ ለሕዝብ ነፃ የሆነው የአንድ ሰዓት ከሩብ መድረኩ ነበር። ምሁራኑና ባላሥልጣናቱ፤ ሙሉውን ቀን፤ የዝግ ስብሰባ ሲያደርጉ ከዋሉ በኋላ ነው ይሄን ለሕዝብ ነፃ የሆነ መድረክ ያዘጋጁት። በዝግ ስብሰባቸው ላይ ምን እንደተነጋገሩ ማወቅ አይቻልም። በዚያ ላይ ዝርዝር ከመነጋገር ሌላ፤ ለነፃው መድረክ፤ ማን ምን ማቅረብ እንዳለበት ተዘጋጅተዋል የሚል ዕምነት አለኝ። በተጨማሪም ለመንግሥታቸውና ለተቋሞቻቸው የሚሆን የአቋም መግለጫ እንደሚያዘጋጁም እምነት አለኝ። ሆኖም ጨረፍታውን ማግኘቱ ቀላል አይደለም።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

የአሁኑ ሀቅ

Map Cartoon አንድ.png

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

Ethiopian Politics, 1991 Revisited

Ethiopian Politics, 1991 Revisited
Continue reading

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

የለውጡ የወደፊት ሂደት

የለውጡ የወደፊት ሂደት

አንዱዓለም ተፈራ

ማክሰኞ፣ መስከረም ፰ ቀን፣ ፳ ፻ ፲ ፩ ዓ. ም. ( 9/18/2018 )

ከመነሻው፤ ለውጡን የምንፈልግ በብዛት እንደምንገኝ ሁሉ፤ ለውጡን የማይፈልጉ ብቻ ሳይሆን፤ ለውጡን የሚቃወሙ እንዳሉ ማመን አለብን። ባሁኑ ሰዓት ለውጡ እንቅፋቶች ገጥመውታል። እኒህ እንቅፋቶች፤ መሠረታዊ ችግሮች ናቸው? ወይንስ በሂደት የመጡና ሊወገዱ የሚችሉ? ለውጡ የጎደለው እንዳለ ጠቋሚዎች ናቸው? ወይንስ የለውጡ ምንነት ችግር? የለውጡ ሂደት የፈጠራቸው ናቸው? ወይንስ ከለውጡ ምንነት ጋር የተያያዙ? ከምን የመጡ ናቸው? ይሄንን ሳይመለከቱ፤ በደፈናው እንዲህ ሆነ እንዲያ እናድርግ በሚል መጓዙ፤ የእምቧለሌ ሽክርክር ይሆናል።

መጀመሪያ ማድረግ ያለብን፤ ለውጡ ለምን መጣ? በማን ላይ መጣ? ማን አመጣው? እንዴት መጣ? የሚለውን መመለስ ነው። አዎ! ችግር አለ። ይሄን መካድ አይቻልም። አዲስ አበባ ውስጥ ሆነ አርባ ምንጭ፣ ኢትዮጵያ ሶማሊም ሆነ ቤንሻንጉል፤ በየቦታው የተፈናቀሉትም ሆነ፤ ሆን ተብሎ የሚዘመትባቸው ሰዎች፤ መሠረታዊ በሆነ ችግር ምክንያት እንጂ፤ ሰዎቹ ስለተጠሉ ወይንም ወንጀል ስለሠሩ አይደለም።

በአንድ ሀገር የሚከሰተው ለውጥ፤ እንዲህ መሆን አለበት! ወይንም እንዲያ መሆን አለበት! ተብሎ በተቀመጠ ቅምር እንደ ተዘጋጄ እጄ ጠባብ፤ የሚጠለቅ አይደለም። ተጨባጩ የሀገሪቱ ሁኔታ፣ የወቅቱ የፖለቲካ ሀቅና፣ በሂደቱ ያሉት ተሳታፊዎች አሰላለፍ፤ ይወስነዋል። ያም እንኳን ሆኖ፤ ለውጡን በትክክል መተንበይ አይቻልም። የኛን እውነታ ስንመለከት፤ ለውጡ ኢሕአዴግ በፈጠረው በደልና ጥፋት የተነሳ የመጣ ነው። ለውጡ ኢሕአዴግን ለማፍረስና፤ ያራመዳቸውን የፖለቲካ ቀውሶች ለማስተካከል ነው። ለውጡን ኢሕአዴግ ሊመራው አይችልም። የመጀመሪያው ችግር፤ ለውጡ የመጣበት ኢሕአዴግ፤ ለውጡን እየመራ መገኘቱ ነው። ይህ ማለት፤ በኢሕአዴግ ውስጥ ያሉ ለውጥ ፈላጊዎች ተሳታፊ አይሆኑም ማለት አይደለም። ነገር ግን፤ እነሱ የለውጡ አካል ይሆናሉ እንጂ፤ የለውጡ ባለቤትና ግለኛ መሪዎች መሆን አይችሉም። ይህ፤ በመፈንቅለ መንግሥት ከሚደረግ የለውጥ ሂደት ጋር ይመሳሰላል። አብዛኛውን ጊዜ፤ የሥርዓቱ ምሰሶ የሆነው ወታደራዊ ክፍል፤ መፈንቅለ መንግሥት ያደርግና፤ “እኔ ባለቤት ነኝ፤ ሌሎቻችሁ አርፋችሁ ተቀመጡ!” ይላል። ይህ ያንን ያስታውሰኛል። ከራሳችን ታሪክ መማር ይገባናል።

ቀጥሎ ደግሞ፤ የለውጡን መሠረታዊ መነሻዎች ወደ ጎን ትቶ፤ ሌሎችን ማስተካከሉ ላይ ነው። ለውጥ ሲደረግ፤ መነሳት ያለባቸው ሰዎች፤ አሁንም አድራጊ ፈጣሪ ሆነው መገኘታቸው ነው። በዐማራው ክልል ሆነ በደቡብ ክልል፣ አሁንም የኢሕአዴግ መሪ የነበሩ ናቸው በማስተዳደርና፤ የለውጡ መሪዎች ነን ብለው ተሰልፈው የሚገኙ። ማገናዘብ ያለብን፤ እኒህ ሰዎች ባሉበት ቦታ ከፍተኛ በደል በሕዝቡ ላይ በደል ፈጻሚ ነበሩ። የተበደሉትና ከፍተኛውን መስዋዕትነት የከፈሉት ናቸው፤ የለውጡ ባለቤቶች። በምንም መለኪያ ቢሆን፤ ለውጡ የመጣባቸው ለውጡን ሊመሩ አይችሉም። አሁን እየታዬ ላለው ሁኔታ፤ ይህ ሀቅ ከፍተኛ አስተዋፅዖ አለው።

ከላይ የተቀመጠው አሁን ያለውን መንግሥት አስመልክቶ ነው። ነገር ግን ያ ብቻ አይደለም ችግሩ። ኢሕአዴግ የሚመራው መንግሥት የሚንቀሳቀሰው፤ በኢሕአዴግ ሕገ መንግሥት ነው። ያ ብቻም አይደለም። ባሁኑ ሰዓት፤ በወታደራዊ ክፍሉ፣ በደህንነት መሥሪያ ቤቱና በመንግሥቱ አጠቃላይ መካከለኛ አመራር ላይ ተሰግስገው የሚገኙት የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር ሰዎች ወይንም እነሱ በገንዘብ የገዟቸው ሰዎች ናቸው። እኒህ ሰዎች ሕልውናቸውን የተከሉት፤ ለትግሬዎቹ ገዥ ቡድን ጥቅም ነው። ዐማራ ሆኑ ሶማሊ፤ ኦሮሞ ሆኑ የደቡብ ክልል ስዎች፤ የሚወክሉት ሕዝብ ኖሯቸው ሳይሆን፤ ለሆዳቸው ለትግሬዎቹ ገዥዎች ተገዝተው የቆሙ ናቸው። እናም አሁን በትክክል የሚወክሉት ሕዝብ የላቸውም። ስለዚህ፤ የሚያገለግሉት ያንኑ አሳዳሪያቸውን ነው። በርግጥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እየወሰዱ ያሉትን ትክክለኛ እርምጃዎች፤ ማድነቅ አለብን። ያ ግን መሠረታዊ አይደለም። የግለሰቦች መልካም ፈቃድ፤ የሀገርን ሂደት ወሳኝ መሆን የለበትም። አሰራሩ ነው ወሳኙ። ለውጡን ያመጣውን ክፍል አግልሎ፤ ወደፊት መሄድ አይቻልም። አሁንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚወክሉት ኢሕአዴግን እና ኦሕዴድን እንጂ፤ የኢትዮጵያን ሕዝብ አይደለም። ውክልና የሠጣቸው ኢሕአዴግ ነው። አሁንም የኢሕአዴግን መዋቅር ነው እየመሩ ያሉት። ይሄ ሁሉ በገዥው ክፍል ላይ ቢነሳም፤ በአንጻሩ ደግሞ አማራጩ ጨለማ ነው።

በተቃዋሚ በኩል እስከዛሬ የነበረውና አሁን በተፎካካሪነት አለን የሚለው ክፍል፤ በጣም በሚያሳዝን ሁኔታ፤ አንድነት የሌለው፣ ግልጥ ራዕይ ያላስቀመጠ፣ አማራጭ ሆኖ ያልተገኘ ነው። ቁጥሩ መብዛቱ ብቻ አይደለም። እያንዳንዱ ድርጅት ራሱን ወደላይ ክቦ፤ ከማንም ጋር ላለመሥራት ችግሮችን ደርድሮ፤ “እኔ ነኝ!” እያለ ሲደነፋ ይገኛል። “ሌሎቹ አይረቡም!” የሚል ጉራም አለበት። ይሄ በሆነበት እውነታ፤ ይህ ክፍል፤ በሥልጣን ላይ ያለውን ክፍል፤ በምንም መንገድ ሊወቅስ አይገባውም። ራሱን አያውቅምና! ብሔራዊ የፖለቲካ ድርጅቶች ባንድ በኩል፤ ሀገር አቀፍ ነን የሚሉ በሌላ በኩል ተኮልኩለዋል። በጣም አጽናፋዊ አቋም ያላቸው፤ ኢትዮጵያዊነትን እርግፍ አድርገው ጥለዋል። በሀገር አቀፍ ዓላማ የተደራጁትም በመካከላቸው የርዕዩተ ዓላማ ልዩነት ሳይሆን የመሪዎች ልዩነት አንቋቸው፤ መቀራረብ አላሳዩም። መሰባሰብ ይጠቅማቸው ነበር። ከሁሉ በላይ ደግሞ፤ ከገዥው ክፍል የሚለዩበትን የርዕዩተ ዓለም ጉዳይ፤ በግልጥ ለሕዝብ አላቀረቡም። የምርጫ ቀን መሆን የለበትም። ከዚያ በፊት፤ ለምን እንደተቋቋሙ መናገር አለባቸው። አማራጭነታቸው የምርጫው ወቅት አይደለም የሚሰመረው። ከዚያ በፊት ከሕዝብ ጋር ሲተዋወቁ፤ ማንነታቸውን መግለጥ አለባቸው። አዎ! የሀገራችን የፖለቲካ ሂደት በየቀኑ እየተለዋወጠ ነው።

ሀገራችን አሁን ካለችበት ወጥታ ወደፊት ለመሄድ፤ ሀገራዊ የሆነ ራዕይ፣ መስማሚያ ጉዳይ፣ አሰባሳቢ መድረክ ያስፈልገናል። ሕዝቡ የኔ የሚለው መንግሥት በቦታው መቀመጥ አለበት። ድክመቱ ያለው በሁሉም ወገን ነው።

አሁን ወዳለንበት ሀቅ ስንመለስ፤ የለውጡ ሂደት እየተካሄደ ያለው፤ የኢሕአዴግ አባል ሆነው፤ ለውጥ እንዲመጣ የሚፈልጉ ጥቂት ግለሰቦች፤ የሚችሉትን በማድረግ ነው። እንግዲህ የለውጡ ግስጋሴና ጥልቀት፣ የለውጡ ፍጥነቱና ይዘቱ፤ በኒሁ ግለሰቦች ፍላጎት ይመራል ማለት ነው። ይህ በጣም ሊያሳስበን ይገባል። ይሄንን ሊያደርጉ የምችሉት ደግሞ፤ የኢሕአዴግ ሕገ መንግሥት በፈቀደላቸው መሠረት መሆኑን ከላይ አስፍሬያለሁ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የታጋዩን ክፍል ልብ ሰልለው፤ “ለውጡ እኔ ነኝ። የማሸጋግርህ እኔ ነኝ። የሽግግር መንግሥቱ እኔ ነኝ! ከፈልግህ ተደራጅና፤ እኔ አስመራጭ፣ ምርጫ አዘጋጅ፣ የምርጫ ሂደቱን ተከታታይ በሆንኩበት ምርጫ፤ የሽግግሩን ዘመን ከጨረስኩ በኋላ ተሳተፍ!” ብለው ቁጭ አሉ።

ወደፊት እንሂድ። አሁን ለውጡን የሚመሩት፤ መጀመሪያ ሕጋዊነት ያግኙ። የኢሕአዴግ ሕጋዊነት በለውጡ እውነትነት ፈርሷል። የሕዝቡን ውክልናን ለማግኘት፤ የፖለቲካ መሠረታቸውን ማስፋት አለባቸው። ይህ ማለት፤ የሕዝቡን ታጋዮች ያካተተ መንግሥት ማለት ነው። ይህ ሰቅዞ ከያዛቸው የኢሕአዴግ ሰንሰለት ነፃ ያወጣቸዋል። ቆራጥ እርምጃ እንዲወስዱ ይፈቅድላቸዋል። ሕዝቡ የኔ ብሎ እንዲከተላቸው በር ይከፍትላቸዋል።

በተፎካካሪው ክፍል ያሉት ደግሞ፤ ትክክለኛ አማራጭ ሆነው መቅረብ አለባቸው። ዓርማ መለጠፍ፣ መርኀ-ግብር ማውለብለብ፣ መሪዎችን ባደባባይ ማዞር ብቁ ድርጅት መኖሩን አያሳይም። መጥቆ የወጣ ራዕይ፣ የተጠናከረ ድርጅትና በዛ ያሉ አባላት፣ የሚመዘን ተልዕኮና በግለሰቦች ፍላጎት ሳይሆን በድርጅታዊ አሰራር የሚመራ የፖለቲካ ድርጅት ሆነው መገኘት አለባቸው። ያ አለ ወይ?

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

በረራ፤ የ፲፭ኛው ከፍለ ዘመንና የ፲፮ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ የነገሥታት ከተማ

Berara - በረራየጽሑፉ ጭምቅ ይዘት፤

በረራ፤ የ፲ ፭ኛው ከፍለ ዘመንና የ፲ ፮ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ የነገሥታት ከተማ (ኢትዮጵያ)፤ በየረር ተራራና ወጨጫ ሸንተረሮች፤ በመካከለኛው ክፍለ ዘመን እና ከዚያ ቀደም የነበረ ሕዝብ ሰፈራ፤ የቅርብ ጊዜ የምርምር ጥናቶች ውጤት፤

ይህ ጽሑፍ፤ የበረራን እና በ፲ ፭ኛው ከፍለ ዘመን እና በ፲ ፮ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ የነበሩ የሰፈራ ቦታዎችን ታሪክኅ ዞሮ ይመረምርና፤ ታሪካዊ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ የሆነችውን በረራን፤ ቦታዋን ለይቶ፤ በደቡብ ሸዋ፤ በአሁኗ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ፤ አዲስ አበባ ከተማ አቅራቢያ፤ መሆኗን ለማመላከት የታሰበውን የመስክ ጥናት ውጤቶችን ይገልጣል። ታሪካዊ ምንጮች እና የሳተላይት የጥልቀት ዕይታዎች፣ የመልክዐ ምድር አቀማመጥ ሁኔታዎች እና ተጨባጭ የአካባቢ መሬት ጥናቶች ላይ በመንተራስ፤ ደራሲዎቹ ወደኋላ ወደ ቅድመ መካከለኛው ክፍለ ዘመን የሚደርሱ የሚመስሉ አዳዲስ ቦታዎችን በማሳወቅ፤ ረጅሙን እና የኢትዮጵያ የዚህ አካባቢ አስካሁን ያልታወቀ ታሪክ አሳይተውናል። ሆኖም ግን፤ በረራን በትክክል ቦታው ላይ ማስቀመጡ አዳጋች ሆኗል። እናም የመካከለኛው ዘመን በኢትዮጵያ የክርስቲያን “ከተሞች” ዕውቀታችን እንዲዳብርና እስካሁን በትክክል ያልተጠናውን ለሕዝቡና ለባህሉ እንቅስቃሴው ማዕከላዊ የሆነውን የዚህ አካባቢ የቅድመ መካከለኛው ዘመን ታሪክ እንዲገልጥልን፥ ተጨማሪ ጥናቶች ያስፈልጋሉ።

( ሙሉውን በፒዲኤፍ ለማንበብ ይሄን ይጫኑ –>  የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጥራዝ ፪ ሺህ ፩ – ፪ ቅጽ ፳፬, ገጽ ፪፻፱ እስከ ፪፻፵፱

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

ወደ ፊት ለመሄድ

አሁን ካለንበት ተነስተን ወደፊት ለመሄድ፤ የግድ የነበርንበትን ማወቅ አለብን። የነበርንበትን ማወቅ የምንችለው፤ ታሪካችንን ስናጠና ነው። ታሪካችንን የምናጠናው፤ ከዚያ በጎው ከሆነውም ሆነ በጎ ካልሆነው ትምህርት ለመውሰድ ነው። ታሪካችንን ካላጠናን፤ ከዚያ የነበረውን ስህተት አንማርበትምና ልንደግመው እንችላለን።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

ዐማራው ያለበት ሁኔታና የወደፊት ጉዞው አቅጣጫ ( ክፍል ፩ )

ዐማራው ያለበት ሁኔታና የወደፊት ጉዞው አቅጣጫ ( ክፍል ፩ )
አንዱዓለም ተፈራ
ነሐሴ ፰ ቀን ፳ ፻ ፲ ዓ. ም.

ከምን ተነሳን? ( የመጀመሪያው ጉዳይ )

ዐማራው አሁን ያለበት ሁኔታ፤ እስከዛሬ ከደረሰበት በደል የተነሳ የወደቀበት አዘቅት ነው። ይሄን ረግጦ በመነሳት፤ ወደፊት ጥሶ መሄድ ያስፈልጋል። ስለፈለጉ ብቻ ግን፤ ወዳሰቡት ቦታ መሄድ አይቻልም። መመርመር አለ። ማቀድ አለ። ማመቻቸት አለ። መተግበር አለ። ይህን ሂደት፤ መመርመሩን እና ማቀዱን፣ ማመቻቸቱን እና መተግበሩን፤ ከኛ ውጪ ላሉ፤ ለሌሎች መሥጠት አንችልም። እኛው ራሳችን፤ የኛ የራሳችን ጉዳይ ነው ብለን፤ ባለቤትነቱን ወስደን፤ ተግባር ላይማዋል አለብን። በኔ በኩል፤ ከዚህ በማከታተል፤ የነበረውን ተመልክቼ፣ አሁን ያለንበትን አካትቼ፣ ወደፊት ልንጓዝ ወደ ምንፈልገው ግባችን የሚወስደንን መንገድ ተልሜ፤ አሁን ማድረግ ያለብንን እጠቁማለሁ።

የዐማራው የሕልውና ጉዳይ መልክ ያበጀው፤ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር፤ ገና ሲመሠረት፤ “በዐማራው መቃብር ላይ፤ የትግራይን ሩፑብሊክ እመሠርታለሁ!” ብሎ በወረቀቱ ላይ ያሰፈረ ጊዜ ነው። ከዚያ ቀጥሎም በ፲ ፱ ፻ ፸ ፪ ዓ. ም. ተከዜን ተሻግሮ ወልቃይት ሲገባ፤ ሕዝቡን ስብስቦ፤ “ከዛሬ ጀምሮ እናንተ ትግሬዎች ናችሁ! የምትናገሩት በትግርኛ ብቻ ነው! የምታለቅሱት በትግርኛ ብቻ ነው! የምትዘፍኑት በትግርኛ ብቻ ነው! አቤቱታችሁን የምትጽፉት በትግርኛ ብቻ ነው። የምትጽፉትም ለኛ ብቻ ነው!” የሚል አወጀ። ወልቃይትን ከ፲ ፱ ፻ ፸ ፪ ዓ. ም. ጀምሮ፤ በአዋጅ ትግራይ አደረጋት። አውራ ላይ ከኢሕአፓና ከሕዝቡ ትልቅ ጦርነት ገጠመው። ወጣት የትግራይ ልጆችን ማገደ። ነገር ግን፤ ኃላፊነቱ ለወጣቱ ነፍስ ሳይሆን፤ ለዓላማቸው ነበርና፤ የማገደውን ማግዶ ወልቃይትን ተቆጣጠረ። ወደ ጠለምት አመራ።

በዚህ ጊዜ፤ የጠለምት፣ የብራ ዋስያ፣ የወልቃይትና የጠገዴ አርበኞች፤ “እኛ አርሶ አደሮች ነን። መንግሥት ከሆናችሁ፤ ዋና ከተማውን ያዙና፣ ከዚያ ሆናችሁ ስትጠይቁን፣ ግብራችን እንልካለን። በዚህ በቦታችን ግን ተውን! እኛ ማንነታችንን ራሳችን እናውቃለን! ሌላ ሰው ማንነታችን አይነግረንም! እኛ ትግሬዎች አይደለንም! እኛ ዐማራዎች ነን!” በማለት፤ “ከፋኝ!” ን አቋቁመው፤ ትግላቸውን ጀመሩ። በቀጥታ ማጥፋት ስላልቻለ፤ በካህናት ልመናና ሽምግልና በማባበል፤ የመጀመሪያውን መሪ፤ ገብረመድሕንን በዕርቅ አባብሎ አስገብቶ ገደል። በመቀጠል፤ ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ፤ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ መንግሥት የሚያደርገውን ግፍና በደል በመቃወም፤ ሕዝቡን መቀሰቀስ ሲይዙ፤ ኢትዮጵያ የብሔርና ብሔረሰቦች ስብስብ እንጂ፤ ኢትዮጵያዊ የሚባል ሕዝብ የለም ስለተባሉ፤ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያሰቡትን ተገደው፤ የመላ ዐማራ ሕዝብ ድርጅትን በማቋቋም፤ ትግላቸውን ገፉ። ነገር ግን፤ ከሁሉም በላይ ዐማራውን ይፈራ የነበረው የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር መንግሥት፤ የዐማራውን ትግል ለማጥፋት እሳቸውን መግደል አስፈላጊ ነው ብሎ በማመን፤ እሳቸውን ለሞት ዳረጋቸው።

የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር፤ በመርኀ-ግብሩ እንዳሰፈረው፤ ዐማራውን ማጥፋት ዋና ጉዳዩ ነበርና፤ ባቋቋማቸው ተቀጥላ የብሔር ድርጅቶቹ አማካኝነት፤ የራሱን መንግሥት ሲያቋቁም፤ ዐማራው ያላተሳተፈበት ሕገ-መንግሥት አረቀቀ። በሕገ-መንግሥቱም ዐማራው ስፍራ እንዳይኖረው ተደረገ። ዐማራው በዐማራነቱ የሕዝብ ጠላት ተደረገ። ከየመሥሪያ ቤቱ ተባረረ። የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር በአጠራቸው ክልሎች ውስጥ፤ ዐማራው እንዲጨረስ፤ በአሽከሮቹ በነ ታምራት ላይኔ አማካኝነት፣ ተገደለ፣ ተፈናቀለ፣ ተሰደደ፣ ተዘረፈ፣ ታሰረ፣ የሁለተኛና የሶስተኛ ደረጃ ዜግነት እንኳን ተነፈገው። ከ “ደቡብ ኢትዮጵያ” ከ “ኦሮሚያ” ከ “ኢትዮጵያ ሶማሊያ” ከ “ትግራይ” የዐማራ ሰው እንዳይገኝ ተገፋ። ይብስ ብሎ፤ በራሱ በ “ዐማራ” ክልልም የትግሬዎቹ የበላይነት ነገሠበት። ዐማራው ቤት የሌለው ሆነ። በደል ምን ጊዜም በደሉን የሚቃወም ያፈራልና፤ ዐማራው በእምቢተኝነት ትግሉን ሳያባራ ቀጠለ።

በከፋኝ የጀመርነው ሰዎች፤ በራሳችን ድክመትና በሁኔታው አለመመቸት፤ ስንከፋፈልና ስንነቃቀፍ፤ መሸናሸንና መበታተን ተከተለን። ፕሮፌሰር አስራትም ከዕረፍታቸው በኋላ፤ ትክክለኛ መሪና ትክክለኛ መርኅ ባለመኖሩ፤ መዐሕድ ተዳከመ። ይሄም ሆኖ፤ ባንድ መልኩም ሆነ በሌላ፤ የዐማራው ትግል አልቆመም። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አዲስ ክስተት ተፈጠረ። በወያኔ አገዛዝ ውስጥ ያደጉ ትንታግ የዐማራ ወጣቶች፤ የዐማራ ብሔርተኝነትን በማንገት፤ ቤተ ዐማራ ብለው ብቅ አሉ። እኒህ ወጣቶች፤ አዲስ ፈር ቀደው፣ ወጣቱን በራሱ እንዲተማመን ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል። የኛው አባዜ አልለቃቸው ብሎ፤ ባንድነት እንደጀመሩት መቀጠል አቅቷቸው፤ እነሱም በመከፋፈል ተዳከሙ። የጀመሩት የዐማራ ብሔርተኝነት እንቅስቃሴ ግን አልበረደም።

እንግዲህ በዚህ ሁሉ አልፈን ነው እዚህ የደረስነው።
እዚህ አሁን ያለንበትን ሁኔታ በሚቀጥለው በክፍል ፪ አቀርባለሁ።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

እና ዐማራ!

እና ዐማራ!
አንዱዓለም ተፈራ
አርብ፣ ነሐሴ ፬ ቀን፣ ፳፻፲ ዓመተ ምህረት

ለውጡ እስካሁን በጀመረው መንገድ ይሄዳል የሚል ተስፋ ሁላችን ሰንቀናል። ባሁኑ ጊዜ፤ መሠረታዊ የሆኑት የኢሕአዴግ የአስተዳደር መተክሎቹ እንዳሉ ናቸው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲናገሩ፤ የዘር ፖለቲካው ባጭር ጊዜ ውስጥ እንደማይለውጥ አስምረውበታል። ከውጪና ከውስጥ የዘር ፖለቲከኞች የሰላ የመቀራመቻ ስንጢያቸውን አሰልስለው “የኔ!” “የኔ!” ታቸውን ተያይዘውታል። በዚህ ሂደት አንድነት የሌለው የዐማራው የድርጅቶች ጋጋታ፤ ቁጥሩ የሚጨምርበት እንጂ፤ ወደ አንድ የሚሰባሰብበት ሁኔታ አይታይም። እና ዐማራ!

የሾህ አጥር በመካከላችን ማበጀቱን ትተን፤ ይሄን ጉዳይ የሁላችን አድርገን መነጋገር እንችላለን። የዐማራው ጉዳይ የእከሌ ወይንም የእከሊት አይደለም። የሁላችንም ነው። የአንድ ድርጅት ወይንም የሌላም አይደለም። የዐማራዎች በሙሉ ነው። ይሄን ጉዳይ ደግሞ ካልተነጋገርንበት፤ ሌላ ከዚህ የከበደ ምን አለ? ሀቁን መመልከትና እውነቱን መነጋገር አለብን። በዐማራው ላይ የተደረገው ጭፍጨፋ፤ በዐማራነት እንጂ፤ ግለሰቦች በሠሩት ተግባር የተመሠረተ አይደለም። ይህ ሆን ተብሎ ታምኖበትና በመምሪያ በተግባር የዋለ በመንግሥት ደረጃ የተከናወነ ጥፋት ነው። እናም ዐማራ የሆን ሁላችን፤ ልንቆረቆርበት ይገባናል። ባሁኑ ሰዓት የዐማራውን የፖለቲካ ምህዳር አጣበው የያዙት፤ የብሔረ ዐማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብዐዴን) እና የዐማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (ዐብን) ናቸው። የዐማራ ጉዳይ ደግሞ፤ የብዐዴን ወይንም የዐብን ብቻ፤ የግል ጉዳይ አይደለም። የብዐዴን አመራር፤ ከመካከለኛው መንግሥት ጋር ሆኖ፤ ሀገር የመምራትና ሀገር አቀፍ ፓርቲ የመመሥረት ዓላማ ያለው ይመስላል። ዐብን ደግሞ፤ እኔ ነኝ የዐማራ ብሔርተኝነት ማዕከል ብሎ፤ በብቸኝነት ቢሮዎቹን በየቦታው በመክፈት ላይ ነው። የነኝህ የየራሳቸው ሩጫ፤ ዐማራውን ይጎዳዋል። እኒህ ሁለቱ፤ አንዳቸው አንዱን አጽናፍ፤ ሌላቸው ሌላኛውን አጽናፍ ይዘው የሚጓተቱበት መሆን የለበትም። ሁለቱም በየበኩላቸው የየራሳቸው ጥናካሬና ድክመት አላቸው። በኔ በኩል፤ እኒህ ሁለቱ ቢጣመሩ ጥንካሬያቸው አይሎ፤ ሁሉን ዐማራ ሊወክሉ የሚችሉበት ሁኔታ ይፈጠራል እምነት አለኝ።

የዐማራ ሕዝብ አንድ ነው። ለዐማራው የሚቆም ደግሞ ባንድ መሰለፍ አለበት። ይህ ለዐማራው መቆም፣ የርዕዩተ ዓለም ባለቤትነትን አይጠይቅም፣ አያካትትም፣ አያስፈልገውም። ይህ ለአንድ ወገን የመቆርቆር ጉዳይ ነው። ተቆርቋሪዎች ደግሞ፤ በሙሉ በአንድነት ተሰባስበው መመካከር አለባቸው እንጂ፤ ወዲያና ወዲህ ሆነው መጓተት የለባቸውም። ከዚህ በመነሳት፤ ለዐማራው እንቆማለን ያሉት በሙሉ፤ የየድርጅታቸውን ጥንካሬም ይሁን ድክመት ሳይመዝኑ፤ ለዐማራው መቆም አለባቸው። እናም አንድ የዐማራ ጠንካራ ድርጅት ነው የሚያስፈልገው። ብዐዴንና ዐብን ወደ አንድ መምጣት አለባቸው ስል፤ ከዚህ እምነት በመነሳት ነው። ለምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮነንና ለዐማራው ፕሬዘዳንት ገዱ አንዳርጋቸው፤ ከኦሕዴድ በፊት፤ አብን ይቀርባቸዋል። ከኦሕዴድ ጋር ከመደራደራቸው በፊት፤ በዐማራው በኩል ያለውን በአንድነት ቢመሩት፤ ለራሳቸውም ጥንካሬ፤ ለዐማራውም ትክክለኛ ውክልና ይኖራል።

የሁለቱን ድርጅቶች ድክመት እዚህ ላይ ማተቱ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ስለሚያይል አልሄድበትም። ጥንካሬያችውን ስንመለከት ደግሞ፤ በብዐዴን በኩል፤ መንግሥታዊ መዋቅር፣ ንብረትና ግዝፈት አለው። በዐብን በኩል ደግሞ ወጣቱ፣ የጠነከረ የዐማራነት ብሔርተኝነትና ትኩስነት አላቸው። እኒህ የሁለቱ ወገኖች ጥንካሬዎች ባንድ ላይ ሲጣመሩ፤ ከፍተኛ የሆነ የደቦ ጉልበት ይፈጥራሉ። በሕዝቡ ዘንድ ደግሞ ቀስቃሽ ስሜትን ፈጥሮ፤ ብዙዎችን ያነሳሳል። እስኪ በያላችሁበት ይሄን ምከሩበት።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ