ድልድይ የሌለው ተቆርቋሪነት

ድልድይ የሌለው ተቆርቋሪነት
አንዱዓለም ተፈራ
ማክሰኞ፤ ነሐሴ ፩ ቀን ፳ ፲ ዓመተ ምህረት

ድልድይ ሁለት ጎን ለጎን የሆኑ ቦታዎችን ያገናኛል። ድልድይ በሌላቸው ቦታዎች የሚገኙ ሰዎች፤ መገናኘት ያስቸግራቸዋል። ባንጻሩም፤ ከትናንት ወደ ዛሬ የሚያሸጋግር ድልድይ ከሌለ፤ ዛሬ ትናንት የተሠራውን እንደገና እንዳዲስ በመሥራት ይጠመድና፤ ዛሬ ሁልጊዜም ትናንትን እንደሆነ ይቀጥላል። ይህ ነው በኢትዮጵያ፤ ለሕዝብ ተቆርቋሪዎች የእንቅስቃሴ ሂደት፤ በተደጋጋሚ እያየን ያለነው። ከትናንት መማር እያቃተን፤ ዛሬም የትናንቱን መልሰን ስንዳክርበት እንገኛለን። ለምን? መማር ስለማንችል አይደለም። የትናንቱ ስላልተመዘገበም አይደለም። የማስተላለፉ ሥርዓት በትክክል ስላልተከናወነ ነው። የዚህ ጽሑፍ ማጠንጠኛ ይህ ነው።

ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነኝ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ፤ “በአቸነፈ እና በአሸነፈ የተላለቃችሁ!” ብለው ያስቀመጡትና አዳራሹን የሞላው ያጨበጨበበት፤ ብዙ ሕይወት ያለፈበትን የሁለት የተለያዩ የፖለቲካ አሰላለፎችን ትግል አቅልለው በማስቀመጣቸው ቢሆንም፤ ይህ የግል ስህተታቸው ሳይሆን፤ በብዙኀኑ ተቀባይነት ያለው መሆኑ ነው። አጨብጫቢዎቹ ስለ ነበረው ትግል ያላቸው ዕውቀት አነስተኛ ነው። በስድሳዎቹ የነበርነው ተማሪዎች፤ ስለ ሀገራችን ታሪክ፣ ስለ አርበኞቻችን ተጋድሎ፣ ስለ መንግሥት ሂደት፣ ስለ ታሪክና ማንነት የነበረንን ዕውቀት በግሌ ስመለከተው፤ ጎደሎ ነበር። እንዲሆን የምንፈልገውን፤ ከሀገራችን ታሪክና ተጨባጭ እውነታ ጋር አላጋባነውም ነበር። እዚህ ላይ፤ እኔ ሁሉን ወክዬ ሳይሆን፤ በግሌ ሁን የማምንበትን ነው የማስቀምጠው። እናም በተማርነው መሠረት፤ ለሁሉም ነገር ፊታችንን ያዞርነው ወደ ውጪ ነበር። ከትናንታችን የወረስነው አጥተን ሳይሆን፤ በቀጣይነት ያስረከበን ድልድይ አልነበረውም። ይህ ትልቅ ስህተት መሆኑን አምናለሁ።

ደርግ፤ ከትናንት የኢትዮጵያ ሕዝብ ተቆርቋሪዎች ለዛሬዎቹ ምንም ዓይነት መወራረስ እንዳይኖር፤ ትውልዱን ጨረሰው። የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ አነጋገር፤ በዚያ ወቅት ደርግ ባደረገው የትውልድ መጨረስ፤ በተተካ የፈጠራ ትረካ ውጤት ነው። መተላለቁ፤ በአንድ ቃል ሁለት አጠራር ላይ የተመሠረተ አልነበረም። መግለጫውን እንደ ዋናው ቁም ነገር መውሰድ፤ ስህተት ነው። ከዚያ በኋላ የተከተለው የፖለቲካ ታጋይም ሆነ የተማሪ ተንቀሳቃሽ፤ ሀ ብሎ እንደገና መፍጠር ነበረበት። ልምዱም ሆነ ግኘቶቹ ለቀጣዩ ትውልድ አልተላለፉለትም። ጉድለቶቹም ሆነ ጥንካሬዎቹ በትክክል አልተነገሩትም። በዚያው በደርግ ጊዜ የተደረጉት ግድያዎችና የቀይ ሽብር ዕልቂቶች በትክክል ተመዝግበው አልተላለፉም። የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር ዙፋኑን ዘርፎ፤ ራሱ ያደረጋቸው ጭፍጨፋዎችና ግድያዎች፤ አሁንም ሳንማርባቸው ተድበስብሰው ወደፊት መቀጠሉ፤ እየተንደረደርንበት ስለሆነ፤ ትምህርት ሳናገኝ፤ ነገ እንዳይደገም ሰግቻለሁ።

አዲሱ ወጣት፤ አዲስ ትግል ብሎ፤ እንደገና ከ ሀ እየጀመረ መቀጠሉ፤ ወደፊት የሚባል ሳይሆን፤ ባለህበት እርገጥ የሚል ጉዞ ላይ ያስቀምጠናል። ከትናንቶቹ በጎ የሆኑና ግድለቶች አሉ። ያን መርምረን፤ ከዚያ መማር ካልቻልን፤ የዚያ ጊዜ ድከመቶችን ተሸክሞ መጓዝና መድገሙ አይቀሬ ነው። ለምን? የስድሳዎቹ ተማሪዎች እንቅስቃሴ መሪዎች ምን ጥሩ ነገር ሠሩ? ምንስ ድክመት ነበራቸው? ከነሱ በፊት የነበሩት ምሁራንስ? ደርግስ? የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባርስ? ነገ የሚከተለውስ? ያን ማሰብና መመርመር ካልቻልን፤ በድክመቶቻቸው ተዘፍቀን፤ ያንኑ እያሸተትን፣ ከዚያው የማንወጣ እንሆናለን።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

የለውጡን መሠረታዊ ምክንያትና ዓላማ መሳት የለብንም።

የለውጡን መሠረታዊ ምክንያትና ዓላማ መሳት የለብንም።

አንዱዓለም ተፈራ
አርብ፣ ሐምሌ ፳ ፯ ቀን ፳ ፻ ፲ ዓመተ ምህረት ( 8/3/2018 )

አለባብሰው ቢያርሱ፤ ባረም ይመለሱ!

አሁን በሀገራችን ውስጥ እየተካሄደ ያለው ለውጥ፤ በተለይ በዐማራ፣ በኦሮሞ፣ በኢትዮጵያዊ ሶማሊ ወጣቶች፤ ባጠቃላይም በኢትዮጵያ ሕዝብ ከፍተኛ መስዋዕትነት የተገኘ ነው። ይህ ለውጥ፤ ኢሕአዴግ መራሽ አይደለም። ይልቁንም ለውጡ በኢሕአዴግ ላይ የተነሳ ነው። የለውጡ ዒላማ፤ ኢሕአዴግና የኢሕአዴግ የፖለቲካ ፍልስፍናና የአስተዳደር መመሪያ ናቸው። ኢሕአዴግ፤ የመለስ ዜናዊ፣ የበረከት ስምዖን፣ የሺፈራው ሽጉጤ፣ የአብዲ ኤሊና አሁንም በየቦታው ተሿሹመውና በወታደሩም ውስጥ በጄኔራልነታቸው ብዙውን የሀገራችንን ሀብት እየተቆጣጠሩ ያሉት፤ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር መሪዎች ድርጅት ነው። ወጣ ካለም ለነሱ ሲያገለግሉ የነበሩ አድር ባዮች የተሸከሙት ድርጅት ነው። ይህ ነው ሕዝብን ያፋጀ፤ በሙስናና በአድልዖ የተሞላ፣ የአንድ ወገኑ የኢሕአዴግ ሥርዓት። ይህን ነው የኢትዮጵያ ሕዝብ በቃኝ ያለው። የለውጡ መሠረታዊ ምክንያትና ዓላማ ይህ ነው።

አሁን ፈጠው ያሉት ጥያቄዎች ግልጥ ናቸው። አንደኛ ለውጡን ያልፈለገው አምባገነኑ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር፤ መቀሌ መሽጎ፤ አሁንም ዘረኛና ለትግራይ ሕዝብ አደገኛ የሆነ ዝግጅት ይዟል። በሌላ በኩል፤ አዲስ አበባ ኢሕአዴግ ለውጥ እያካሄደ ነው። ማለትም ኢሕአዴግ በኢሕአዴግ ላይ ለውጥ እያካሄደ ነው። ዋናው ጠላት መቀሌ ላይ መሽጎ ለውጡን ለማደናቀፍ የሚችለውን ያህል ሁሉ እየሸረበ ያለው የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር ነው። በዚህ ላይ ምንም ዓይነት ብዥታ ሊኖር አይገባም። ይሄን ክፍል ጠላቴ ብሎ የፈረጀው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው። እናም ለውጡን መምራትም መግፋትም የሚችለው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው። ለውጡን ያመጡትና ከፍተኛውን መስዋዕትነት የከፈሉት ተመካች እንዲሆኑ ጥሪ ቀርቦላቸዋል። ማን ባመጣው ለውጥ ነው፤ ማን ተመልካች የሚሆነው? ማን እንዲወገድ ነበር፤ ብዙዎቹ ሕይወታቸውን የገበሩት? ይህ ማለት፤ በትግሉ የተሳተፉትና ግንባር ቀደም ሆነው የተደራጁ ወገኖች፤ ለውጡን ከሚፈልገው የኢሕአዴግ ክፍል ጋር በመሆን፤ ትክክለኛ ለውጥ እንዲመጣ፤ አብረው የሽግግር ወቅቱን መምራት አለባቸው።

መመንጠር ያለበት፤ በኢሕአዴግ ውስጥ ያለው የሕዝብ ጠላት ነው። ይህ ደግሞ በትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር ውስጥ ብቻ ሳይሆን፤ በሌሎቹን ይህ ቡድን በመሠረታቸው የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች ውስጥም ነው። አለባብሰው ቢያርሱ ባረም ይመለሱ እንዳይሆን! ለኔ እስካሁን ጥሩ ተሠርቷል። በዚህ ግን ብዙ መሄድ አይቻልም። ለውጥ አምጪው ክፍል የተሳተፈበት ብቻ ነው፤ ትክክለኛና ዘለቄታነት ያለው ለውጥ የሚያመጣው። ሀገራችን ደግሞ፤ ላለፉት አርባ አምስት ዓመታት ብዙ ደምታለች። ደሙ ያብቃ። የተወሰኑ ሰዎች ሀገር ቤት ለመግባት በመጓጓት የሀገራችንን የፖለቲካ ማህደር ቢኳኩሉት፤ መልኩ እንጂ ውስጣዊ ይዘቱ አይቀየርም። አሁን መሠረታዊ ለውጥ ሥር እንዲሰድ አመቺ ሁኔታዎች አሉ። ለዚህ የለማ ቡድን ምስጋና ይገባዋል። ነገር ግን የለማ ቡድን እየመራው የሚካሄድ ከሆነ፤ ዘለቄታ የለውም። የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚመራውና የሚሳተፍበት መሆን አለበት። ይህ ለውጥ ከዚህ ቡድንና ከኢሕአዴግ በላይ ነው። እናም የሽግግር መንግሥት መቋቋሙ የግድ አስፈላጊ ነው።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

በግለሰብ መተማመን ወይንስ በአሰራር?

በግለሰብ መተማመን ወይንስ በአሰራር?

አንዱዓለም ተፈራ

ረቡዕ፣ ሐምሌ ፳ ፭ ቀን ፳ ፻ ፲ ዓመተ ምህረት ( 8/1/2018 )

ሁላችንም ደስ በሚል ሁኔታ ላይ ነን። በዚህ ሰዓት፤ “ጠንቀቅ እንበል”! ማለቱ የሚያስበረግጋቸው ይኖራሉ። ነገር ግን፤ ዘለቄታ መፍትሔ የሚገኘው፤ ለመፍትሔው አምድና መሠረት የሆነ አሰራር፤ በቦታው ሲኖር ስለሆነ፤ የግድ ጠንቀቅ እንበል። ሰዎች ይመጣሉ፤ ሰዎች ይሄዳሉ። ዛሬ የወደድነውን ግለሰብ፤ የወደድንበት ምክንያት የሚለወጥበት ሁኔታ ሲገኝ፤ ነገ መልሰን ከወዳጅ መዝገባችን እናወጣዋለን። ይህ የኅብረተሰብ ሀቅ ነው። እንግዲህ እዚህ ላይ፤ “በግለሰብ መተማመኑ ነው ወይንስ በአሰራር የተቀመጠ መፍትሔ፤ ዘላቂነት ያለው?” ለሚለው ጥያቄ፤ ምን መልስ እንሠጣለን? ይህ ነው የዚህ ጽሑፍ ማሽከርከሪያ።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ የያዙት አቅጣጫ በጣም ደስ ይላል። በአሜሪካ ያደረጉት ጉዞም የተሳካ ነበር። ይህ ስኬት፤ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ የግል ስኬት፣ ወይንም የለማ ቡድን የግል ስኬት ሳይሆን፤ የመላ ኢትዮጵያዊያን ስኬት ነው። ሁላችን የምንፈልገው፤ ይህ ስኬት፤ ዛሬ ሆነ ነገ፣ በሀገር ውስጥ ሆነ ከሀገር ውጪ፤ ዘለቄታነት እንዲያገኝ ነው። ዘለቄታ የሚኖረው ደግሞ፤ ጉዳዩን ለአንድ ግለሰብ ወይንም ቡድን ፈቃደኝነት በመተው ሳይሆን፤ መደረግ ያለበትን ሁላችን ባንድነት ስናዜመው ነው።  ይህ ዜማችን አሰራርን ይወልዳል። አሰራር ደግሞ ለዘለቄታነት መንገድ ይጠርጋል።

ሀገራችን አሁን ላለችበት ሁኔታ፤ ቀጥተኛ ተጠያቂው ኢሕአደግ እና ኢሕአደግ በቦታው ያስቀመጠው የፖለቲካ ፍልስፍናና የአስተዳደር መመሪያው ነው። ኢሕደግ ቆስሏል። ኢሕደግ ግን አልፈረሰም። ሕይወቱ ብቻ ሳይሆን፤ ፍልስፍናው፣ አስተዳደሩ፣ በሂደቱ ያስቀመጠው ሙስንና የዘር አድልዖ አሰራር፤ በቦታው እንዳለ ነው። የሀገሪቱ ደንበርና ያላግባብ ከሕዝብ የተነጠቀው ለም መሬት፣ በሕዝቡ መካከል የተፈጠረው አለመተማመንና መበላላት፣ የተገደሉ ወገኖቻችን፣ የተፈናቀሉና የተሰደዱ ወገንቾ፣ ተሟጦ የተወሰደው የሕዝብ ንብረት፣ ወዘተ. ብዙ ኢሕአዴግ የሚጠየቅባቸው ጉዳዮች አሉ። በኢሕአደግ ላይ ሕዝቡ ያለው እምነት ራሱ ለጥያቄ የሚቀርብ ነው። ይህ ካልተመለሰ ደግሞ፤ መልካም አስተዳደርና መልካም ተስተዳዳሪ ማሰቡ ያዳግታል። ከሁላችሁም ጋር እስማማለሁ! አሁን ለዚህ ሁሉ መልስ የምንሠጥበት ጊዜ አይደለም። ይህ ጊዜ ይፈጃል። መልካም! ነገር ግን አሁን ካላንበት ወደፊት ለመሄድ፤ መንገዳችን በየት በኩል ነው? ይህ መመለስ አለበት። አቅጣጫና ጉዞው መጀመር ያለበት፤ አስራሩ ዛሬ በትክክል በቦታው ሲቀመጥ ነው።

እዚህ ላይ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ቅንነትና በጎ እምነት አይደለም እየተጠየቀ ያለው! በዋሺንግተን ከተደረገው ስብሰባ፤ ጎደለ የምለው ቢኖር፤ በምሁራን እና በጠቅላይ ሚንስትር አቢይ አሕመድ መካከል የተደረገ ውይይት፤ የሀገራችንን የወደፊት አቅጣጫ የሚያመለክት አለመሆኑ ነው። በርግጥ በዝርዝር ይሄ ይሆናል፤ እንዲህ ይደረጋል የሚል ባልጠብቅም፤ ምን ዓይነት መንግሥት ይቀጥላል? ከምርጫው በፊት፤ የተወዳዳሪዎች ምዝገባና አዘጋጆቹ፣ ይህ የሚካሄድበትን የሚመራው ክፍልና መቼ የሚሉት ጥያቄዎች አለመነሳታቸው ገርሞኛል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ብሩህ ተስፋ አላቸው። መልካም! ታዲያ አግዙኝ ሊሉ እኮ በተገባ ነበር። ምሁራኑ ደግሞ፤ ምን ዓይነት መንግሥት ይዘው ሊገፉ ነው? ብሎ መጠይቅ ነበረበት። ያ አልሆነም። በጄ! እንለፈው። ተስፋ የማደርገው፤ ቢያንስ በጽሑፍ ደረጃ፤ ምሁራኑ ለሳቸው፤ መልካም ትንታኔና መንግሥታዊ ሂደቱን በተመለከተ መደረግ ያለባቸውን የሚጠቁም፤ በተለይ ደግሞ በየሙያ መስካቸው፤ ምን ምን መደረግ እንዳለባቸውና ሀገራችንን የሚያሳድጋትን ሰነድና አቅጣጫ ሠጪ ሰነድ አቅርበውላቸዋል የሚል ነው። አሁን ደግሞ፤ ዛሬ ምን ዓይነት መንግሥት ይዘው ሊቀጥሉ ነው? ይህ የኔ ጥያቄ ነው።

በርግጥ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ፤ አሁን የሚፈልጉትን እየመረጡ፤ ሀገራችንን እየመሩ ናቸው። እሳቸው፣ ኢንጅነር ስመኘው በቀለ እና ሌሎች ቅን የሕዝብ አገልጋዮች በሙሉ ከባድ ፈተና ላይ ናቸው። ኢንጅነር ስመኘው በቀለ በሕይወታቸው ከፈሉ። ጠቅላይ ሚንስትር አብይም ተቃጥቶባቸው ነበር። እኒህ ሁሉ ከለውጡ ጋር በተያያዘ ምክንያት ለመሆናቸው ምስክር ጠያቂ አይኖርም። እናውቀዋለን። ታዲያ ይሄኮ የሁላችን ኃላፊነት ነው። የሳቸው የግል ዕዳ አይደለም። እናም ጊዜው፤ ሰፋ ያለና ሕዝቡን ያካተተ የሽግግር መንግሥት የግድ ይላል። ከላይ እስከታች ሕዝቡ የኔ ብሎ የሚጠብቀው መንግሥት ያስፈልጋል። ይህ ደግሞ የሚሆነው፤ ሰፋ ካለው ኅብረተሰብ፤ በተለይም ከተደራጀው ክፍል ውክልናን ሲያገኝ ነው። የሽግግር መንግሥት ማለት፤ አሁን ካለንበት ወደምንፈልገው ለመድረስ መጓጓዣችን ነው። የሚቀጥለውን ምርጫም አካሂያጁ ይሄው ክፍል መሆን አለበት። ኢሕአዴግ መራጭና አስመራጭ የሚሆንበት ሂደት አጓጉል ነው። ይሄ አቸናፊነቴን ከወዲሁ ተቀበሉ ማለት ነው። በርግጥ ኢሕአዴግ የማቸነፍ ዕድሉ ከማንም በላይ ነው። ነገር ግን እኔው ላዘጋጀው፤ ወይንም እኔ አውቅላችኋላሁና እመድባለሁ ማለቱ አያስኬድም።

ብዙዎች ለዚህ ችግር አይኖርባቸውም። በተለይም እስካሁን ከነበረው ጋር በማነጻጸር፤ ይሄ የተሻለ በመሆኑ፤ በዚህ ብቻ በመርካት፤ የለም አታደፍርስብን! ባዮች አሉ። መልካም! ነገና ከተነገ ወዲያ በተወሰኑ ሰዎች ቅንነት ሀገርን ትመራ ማለት፤ ኃላፊንት የጎደለው ሂደት ነው። ከፋም በጄም አብረን ያደረግነው ጉዳይ፤ ሁላችንን ተጠያቂ ስለሚያደርገን፤ ባለቤትነቱ ሁላችንንም የግድ የተስተካከለ ሥራ እንድንሠራ ያስገድደናል። ሌሎች እንዲሠሩት መተው ግን፤ በኋላ “እነሱ!” እያሉ ጣት ለመጠቆም መዘጋጀት ነው።

እናም የሽግግር መንግሥት መቋቋሙ የግድ አስፈላጊ ነው።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ አውቶቡስና የቅርብ ታሪካችን ትምህርት

የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ አውቶቡስና የቅርብ ታሪካችን ትምህርት

አንዱዓለም ተፈራ

አርብ፣ ሐምሌ ፳ ቀን ፳ ፻ ፩ ዓመተ ምህረት ( 7/27/2018 )

ትናንት አርብ፣ ሐምሌ ፳ ቀን ፳ ፻ ፩ ዓመተ ምህረት ( 7/27/2018 ) ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ከተቃዋሚ/ተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ያደረጉትን ልውውጥ ከድረገጽ ካገኘሁት ቪዲዮ ላይ ተመለከትኩ። ዛሬም በዋሺንግተን ዲ. ሲ. ስብሰባ ያደርጋሉ። ከትናንቱ የተለየ እንደማይናገሩ እገምታለሁ። በአርቡ ስብሰባ፤ ከትንንሽ ድርጅቶች እስከ ትልልቅ ድርጅቶች፣ በዛ ካሉ የብሔር ድርጅቶች እስከ ሀገር አቀፍ ድርጅቶች፣ ከነባር ታጋይ ደርጅት መሪዎች እስከ ነባሮችን ጠይ ድርጅት መሪዋች ድረስ፤ አድናቆት ተቸራቸው። የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ አውቶቡስ፤ ተሳፋሪዎችን ግራና ቀኝ ሲጠራና ሲያሳፍር ተመለከትኩ። አውቶቡሱ ደምቋል። የአረንጓዴ ብጫና ቀይ ሰንደቅ ዓላማ ውስጡን ሞልቶታል።  ኢትዮጵያዊ ቃና ያለው ቅኝት አጥኖታል። ባሁኑ ስዓት ስለ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከታላቅ አክብሮትና ምስጋና በስተቀር፤ አንዲትም ነጥብ በተቃራኒ ማንሳቱ፤ የትየለሌ ጠላትነት ነው። ይህ አንድም ሰማይ! አለያ መሬት! የሚል ሂደት፤ ትክክል እንዳልሆነ እሳቸው ገልጸውታል። እናም እንኳን መንግሥትና ሕዝቡ የምንሰማማበት ወቅት ላይ ደረስን። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ብዙ፤ ብዙዎችን የሚያስደስቱ መልሶች ሠጡ። እኔም ባመዛኙ በመልሶቹ ረካሁ። ከመካከል ግን የቅርብ ታሪካችንን ዞሬ እንድመረምር ያደረጉኝ መልሶችን አገኘሁባቸው። ምንድን ናቸው?

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ፤ በጣም ልብ የሚነካ ቅንነትና ሕዝባዊ ፍቅር አላቸው። የፖለቲካ ግንዛቤያቸውም ካሁን በፊት በመሪዎቻችን ያልታየ ነው። በግለሰብ ደረጃ መደነቅ ያለባቸው ናቸው። ሁላችን መርሳት የሌለብን ደግሞ፤ እሳቸው አንድ ግለሰብ ናቸው። የፖለቲካ ተመክሯቸው ደግሞ፤ አሁን ሊያፈርሱት እርዱኝ! እያሉ ካለው የኢሕአዴግ ሥርዓት የተሸመተ ነው። ከሁሉ በላይ ደግሞ፤ የሀገራችን ችግር በጣም ጥልቅና ውስብስብ ስለሆነ፤ ጊዜ ወሳጅ ነው። እሳቸውም ይሄንኑ አስምረውበታል። በፖለቲካ ሂደት ደግሞ፤ ቋሚ የሆነ ባህርይ የለም። አሰላለፍ በየጊዜው ይቀያየራል። ፊት ለፊት ላጋጠመው የኅብረተሰብ ሁኔታ፤ መፍትሔ የሚሉትን ማቀንቀን የፖለቲካ ሂደት ማሽከርከሪያ ምሰሶው ነው። ዛሬ ጥሩ ያልነው ነገር፤ በቅጽበት ዋጋ ሊያጣ ይችላል። ምን ጊዜም ቋሚ ሆነው የሚቀጥሉት፤ ሕዝቡና ሀገሪቱ ናቸው። አምባገነን መሪዎች በመልክም ሆነ በቅርጽ ከኔና ከርስዎ የተለዩ አይደሉም። ቀንድ የላቸውም። የተለዩ ያገጠጡ ጥርሶችም የሏቸው። ሲጀምሩም፤ “አምባገነን ነኝ!” እያሉ በማወጅ አይደለም። ይሄንን ለማስረገጥ፤ ሩቅ ሳንሄድ፤ የራሳችንን የቅርብ ታሪክ ዞሮ መመልከቱ ይረዳል።

በ ፲ ፱ ፻ ፷ ፮ ዓመተ ምህረት፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዳር እስከዳር አደባባይ ወጥቶ፤ የነበረውን መንግሥት “ወጊድልኝ!” ሲል፤ ተደራጅቶና ታጥቆ የነበረው ወታደራዊው ቡድን፤ “ኢትዮጵያ ትቅደም!” “እናንተ በያላችሁበት አርፋችሁ ተቀመጡ! እኔ ሁሉን አደርገዋለሁ!” በማለት መድረኩን ለብቻው ተቆጣጠረ። አስታውሳለሁ፤ አንድ ወዳጄ፤ “እስኪ ተዋቸው! ጥሩ ይዘዋል! አሁእኛ፤ በየሙያ መስካችን ጠንክረን መሥራት ብቻ ነው ያለብን! እነሱ አንድ በአንድ እያሉ፤ ልክ ያስገቡታል!” ብሎ ተከራከረኝ። እውነትም ሁሉንም ልክ አስገቡት! መሬት!!! ደርጋማው ወታደራዊ መንግሥት፤ ላንድ ሰሞን ጋዜጣዎችን ነፃ አደረገ፡ ውይይት ፈቀድኩ አለና ሰውን አንጫጫ። ከዚያ ለቃቅሞ መሬት አገባቸው። ሰው በላውን መንግሥቱ ኃይለማርያም ለዘለዓለም አንግሦ፤ እኔው ነኝ ሽግግር መንግሥት አለና፤ በበነጋታው እኔው ነኝ መንግሥት ብሎን ቁጭ አለ።

በተመሳሳይ መልኩ፤ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር አዲስ አበባ ሲገባ፤ ብሔሮች ነፃ ወጡ አለን። ከሰው በላው መንግሥቱ ኃይለማርያም አዳንኳችሁ አለን። በደርግ ጊዜ የጠፉት ነፍጠኞች፣ ትምክህተኞችና ፊውዳሎች ነፍስ ዘርተው መጥተው፣ ዓይን አፍጥጠው ተገትረው፣ ክንፋቸውን ዘርግተው ሕዝቡን ካሰሩበት ማነቆ፤ ነፃ አውጣኋችሁ ተባልን። ዴሞክራሲ ነገሰ ተባልን። ኢትዮጵያ ያልነበራት ሕገ መንግሥት አገኘች ተባልን። አዲስ ታሪክ ተጻፈልን። ከዐማራና ለተዋሕዶ በኢተክርስትያን ተላቀቃችሁ ተባልን። ወደፊት ልናይ ነው ተብለን፤ ፊታችንን ወደፊት ስናዞር፤ አንኳንስ ዴሞክራሲ ሰፍኖ አዳዲስ ፓርቲዎች ሊፋፉ፤ አብረው ተማክረው የገቡት የትግራይ፣ የኦሮሞና የኤርትራ ነፃ አውጪዎቹም ተለያይተው ተጨራረሱ። የራሳቸው የሚባል ትውልድ ሰለሌላቸው፤ ያው የፈረደብንን ኢትዮጵያዊያንን በነሱው ጦርነት ማገዱን። ብዙዎች አለቁ። ከዚያማ ሀገራችን እንኳንስ ለውጪዎቹ፤ በውስጥ ላሉት ኢትዮጵያዊያን አዲስ እስከትሆን ድረስ ሁለንተናዋ የተለዋወጠ ኢትዮጵያ ተከሰተች። ባህል፤ ወግ፣ ስነ ሥርዓት፣ ታሪክ፣ በሕዝብ መካከል የነበረው መተሳሰብ ቦታ ተነፈገ።

አሁን፤ በሕዝቡ፤ በተለይም በወጣቱ፤ ከፍተኛ መስዋዕትነት፤ ለዚህ በቅተናል። ታዲያ ከዚህ ወደፊት ለመሄድ ሲታሰብ፤ የት ነበርን? እንዴት ለዚህ በቃን? ወደፊት ለመሄድ አሁን በቦታው ምን አለን? የሚለውን መመልከቱ የግድ ነው። ዝርዝር መግባቱ ቀባሪውን ማርዳት ነው። በቀጥታ ወደ ተነሳሁበት እመለሳለሁ። የመጀመሪያው ለሽግግር መንግሥት ጥያቄ የሠጡትን መልስ በሚመለከት ነው። ሁለተኛው ደግሞ ለዐማራው የሕልውና ጉዳይ የሠጡት ትኩረት ወይንም የትኩረት ማነስ ነው። በየተራ ልሂድባቸው።

የሽግግር ጥያቄ ለምን ተነሳ? ምን ማለትስ ነው?

የሽግግር መንግሥት፤ ከነበረው ወደምንፈልገው ለመሄድ መሸጋገሪያ ድልድዩ ነው። ዛሬ የምንፈልገውን ለማግኘት፤ ያለው ተጨባጭ ሁኔታ፤ የተወሳሰበና ቀና ባለመሆኑ፤ ያንን ለመደልደል እና ለማዘጋጀት፤ የግድ መንገዱን ለማለሳለስ፤ ሁሉም የሀገሪቱ ተቆርቋሪዎች የሚሳተፍበት ቡድን ማዘጋጀት የግድ ነው። አሁን በሥልጣን ላይ ያለው፤ የኢሕአዴግ ፓርቲ ነው። ኢሕአዴግ ራሱን እያሻሸለ ለመሆኑ መስካሪ የሚፈልግ የለም። እያየነው ነው። አሁንም ሀገራችን የአንድ ፓርቲ ሀገር ናት። ምንም ይሁን ምንም፤ ሀገራችን የአንድ ፓርቲ ሀገር ሆና፤ ነገ የብዙ ፓርቲዎች ሀገር ትሆናለች በሚል ተስፋ ወደፊት መሄድ ያዳግታል። ዛሬውኑ ዘለን የብዙ ፓርቲዎች ሀገር ማድረግ አንችልም። ነገር ግን ከአንድ ፓርቲ ወደ ብዙ ፓርቲዎች ለመሸጋገር፤ የግድ የሽግግር ጊዜ ያስፈልጋል። ያ ነው የሽግግር መንግሥት ጥያቄው መሠረቱ። ያንን ዘሎ ማለፍ አይቻልም። ቆዩኝ እኔ አደርገዋለሁ የሚለው ንግግር፣ መንግሥቱ ኃይለማርያምን፣ መለስ ዜናውን ያስታውሱኛል። ያን መስማት ይዘገንናል። የነገዋን ትክክለኛ መንገድ የያዘች ሀገራችን እንድትሆን፤ የግድ የሽግግር ጊዜ ያስፈልገናል። በርግጥ የሽግግሩ መንግሥት አመሠራረትና ይዘት በትክክል መያዝ አለበት። ሆኖም ግን፤ አደጋ አለው! እና ወይንም ሁሉም መንግሥት የሽግግር መንግሥት ነው! የሚለው አያስኬድም። Wንነት ከዚህ ይጀምራል።

የዐማራውን ጥያቄ በሚመለከት፤

ዐማራው እንደሌላው የሀገራችን ሕዝብ ከፍተኛ በደል ተካሂዶበታል። እዚህ ላይ ጥያቄ የለም። የዐማራውን በደል፤ ከጥፋቱ ልክ የለሽነት በላይ፤ ልዩ የሚያደርጉት ግልጽ የሆኑ ኩኔቶች አሉ። በመጀመሪያ ደረጃ፤ ዐማራው በተናጠል፤ “እስከዛሬ በዳይ ሕዝብ ነበር!” በሚል ተፈርጆ ነበር። የትግራይ ነፃ አውጪ ግንባር ገና ሲመሠረት፤ “በዐማራው መቃብር ላይ የትግራይ ሩፑብሊክን እመሠርታለሁ!” ብሎ ነበር የተነሳው። በተግባርም ዐማራውን ከምድረ ገጽ ለማጥፋት ያላደረገው ነገር የለም። ቀጥሎም ያቋቋማቸው ተቀጥላ የፖለቲካ ድርጅቶች በሙሉ፤ ብዐዴንን ጨምሮ፤ ይሄን መተከል የኔ ብለው፤ ዐማራን የዘር ማጽዳት ፈጽመውበታል። ዐማራው በኢትዮጵያዊነቱ አምኖ፤ በመላ ኢትዮጵያ ለምዕተ ዐመታት ኖሯል። ዐማራው ከመላ ኢትዮጵያ እየተፈናቀለ፤ እየተዘረፈ፣ እየተገደለ፣ እየተሰደደ ነበር። ይህ የተለየ በደል፤ አሁንም በግልጽ በራሱ መኖሪያ በሆኑት፤ በወልቃይት፤ በራያ፣ በጠለምት፤ “ትግሬ ነኝ ብለህ ኑር! ወይንም ከዚህ ጥፋ!” ተብሎ ተወጥሯል። መተከል፤ “ያንተ ቦታ አይደለም!” ተብሎ፤ የደረሰበትን በጽሑፍ ማስቀመጡ ይዘገንናል። በዚህ ሁኔታ፤ ሀቁ የሚነግረን ይሄ ሆኖ ሳለ፤ “ሁሉም እኩል ነው!” ብሎ አጨብጭቡና ተደመሩ ብቻ ማለቱ ለኔ አያስኬድም።

ለዐማራው፤ ከሌሎቹ ኢትዮጵያውያን የተለዬ፤ ልዩ የሆነ ሥጦታ ይለገሰው የሚል የለም። ነገር ግን፤ ዐማራው አሁንም የሕልውና ጥያቄ አለው። አሁንም በአደጋ ላይ ነው። በርግጥ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድና መንግሥታቸው ሊያደርጉ የሚችሉት የተወሰነ ነው። አብላጫው ድርሻ፤ ዐማራው ራሱ ሊያደርገው የሚገባው ነው። በወልቃይት፣ በጠለምት፣ በራያ፣ በመተከል የሚኖረው ዐማራ አሁንም በእስር ቤት ውስጥ ነው። የተፈናቀሉ ዐማራዎች አሁንም በየመንገዱ ተጥለው ነው የሚገኙት። ሌላው በሂደት የሚተገበር ይሆናል። ዋናው ግን፤ ይሄን የዐማራውን የሕልውና አደጋ መገንዘብ ነው።

ይሄን ሁሉ ካሰፈርኩ በኋላ፤ አሁንም ለጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ያለኝን አክብሮት መግለጽ እፈልጋለሁ። ሁላችንም እስከዛሬ ይሆናል ብለን ያልገመትነው ገሃድ ሆኖ ስናየው፤ በደስታ መጥለቅለቃችን ያለ ነው። ፊታችንን ስንመለከት፤ ጀርባችንን መዳሰስና የነበርንበትን መፈተሹ፤ ትምህርት ይሠጠናል። ወደን የሰቀልነውን ብቅል፤ ኋላ ማውረዱ እንዳይከብደን፤ ካሁኑ አሰቃቀላችንን እንወቅበት። አመሰግናለሁ። eske.meche@yahoo.com

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

የሽግግር መንግሥት ማቋቋሙ፤ ግዴታ ነው።

የሽግግር መንግሥት ማቋቋሙ፤ ግዴታ ነው።
አንዱዓለም ተፈራ
ሐሙስ፣ ሐምሌ ፲ ፪ ቀን ፳ ፻ ፲ ዓመተ ምህረት

የተራበች እናት ምግብ ማግኘቷ፤ ምርጫ ሳይሆን ግዴታ ነው።
ምርጫ የሚሆነው ሰጪና ነሺ ካለ፤ ለዚሁ አካል ብቻ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ መሐመድ የኦሕዴድ መሪ ናቸው። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ መሐመድ የኢሕአዴግ ወኪል ናቸው። አሁን ኢትዮጵያን እያስተዳደሩ ያሉት፤ በኢሕአዴግ መዋቅርና ሰዎች ነው። በርግጥ የያዙት መንገድ፤ እስከዛሬ በትግሬዎቹ ነፃ አውጪ ግንባር ገዥዎቻችን ሲመራ የነበረው ኢሕአዴግ ሲከተለው ከነበረው ለየት ያለ ነው። አሁንም መሠረቱ ግን ኢሕአዴግና ኢሕአዴግ ሲመራበት የነበረው የፖለቲካ ፍልስፍናና የአስተዳደር መመሪያ ነው። እናም አንድን ወገን ብቻ ወክለው፣ ነገር ግን በጣም ጥሩ ነገር ለብዙኀን በማድረግ ላይ ያሉ ናቸው። ይህ በጎ ተግባራቸው፤ ከመጡበት አኳያ ስናየው ውስንነት አለበት። በአንድ ሰው ቅንነት ሀገር አትመራም። የሚቀጥለው ምንድን ነው? ብለን ከመጠበቅ በላይ፤ ምን መሆን አለበት የሚለውን ሁላችን በያለንበት መነጋገር አለብን። የሀገራችን ችግር ምስቅልቅል ነው። ይህች ሀገር የሁላችን ናት። ለውጡን ተባብረን ቀጣይነቱን ለማረጋገጥ፤ ሁላችን መታቀፍ አለብን።

የሀገራችን ችግር ምስቅልቅል ነው። በቀጥታ አንድና አንድን እንደመደመር ሊወሰድ የሚችል አይደለም። ይሄ ምስቅልቅል ችግር፤ መሠረታዊ የሆነ ከሥሩ መንግሎ የሚጥል መፍትሔ ካልተገኘለት፤ እምቧለሌ ዙሪያ የሚሽከረከርና የማይለቅ ይሆናል። የክልል ጉዳይ አንድ ነው። ከዚሁ ጋር ተያይዞ፤ አከላለሉ፣ አስተዳደሩ፣ “እኛ” እና “ሌሎች” የሚለው ግንዛቤ፣ ርስ በርስ ሕዝቡ እንዲጋደል የተደረገው ሂደት፣ የመፈናቀልና በግፍ የመገደል ጉዳይ ሌላው ነው። አድልዖ፣ ሙስና፣ የመንግሥት ሥልጣንና የተዋረዱ ሂደት ሌላው ጉዳይ ነው። የመንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ የመግባት ሁኔታ፤ ሌላው ጉዳይ ነው። በገፍ ከሀገራቸው የተሰደዱ ኢትዮጵያዊያን ጉዳይ ሌላው ነው። አንዱን አካባቢ ከሌላው አስበልጦ የማሳደግና ዕድሉን ሁሉ በዚያ መንዳት ሌላው ጉዳይ ነው። ብዙ ከዚህ የከፉ ሌሎች ሊዘረዘሩ የሚችሉ እንዳሉ ሁላችን እናውቃለን። የሚከተለው ምንድን ይሆን? ብለን ከመጠበቅ በላይ፤ ምን መከተል አለበት የሚለውን መነጋገር አለብን።

ይህች ሀገር የሁላችን ናት። እናም ሁላችን የኔ ብለን መፍትሔ ማምጣቱ ላይ መረባረብ አለብን። ግዴታውን ለአንድ ግለሰብ ወይንም ክፍል ሠጥተን፤ ሌሎቻችን እጆቻችንን አጣጥፈን መቀመጥ የለብንም። ባለፈው ግማሽ ምዕተ ዓመት በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የደረሰው ጥፋት፤ በኢትዮጵያዊያን የተፈጸመ በመሆኑ፤ የኛው ታሪክ ነው። እናም አብሮን ለምጥ ሆኖ ለዘለዓለሙ ይኖራል። አሁን እንዲቀጥል የምንፈቅድበት ወይንም በትብብር እንዲቆም የምናደርግበት ዕድል ገጥሞናል። ኋላ ዞረን ያኔ እንዲህ ቢደረግ ኖሮ! ወይንም እኔ እንዲያ ባደርግ ኖሮ! ብለን የመቆጫው ጊዜ፤ ሊመጣ አይገባውም። አሁን ማድረግ ያለብንን፤ አሁን ማድረግ አለብን። እናም ትክክለኛው ጥያቄ፤ የሽግግር መንግሥት ይቋቋም ነው።

የሽግግር መንግሥትን መቋቋም የማይፈልጉ አሉ። እኒህ በሁለት ይከፈላሉ። የመጀመሪያዎቹ፤ አሁን ያለውን የለውጥ ሂደት ስለሚጠሉት፤ እንዲከሽፍና የነበሩበት መንበር እንዲመለስላቸው የሚደክሙት ናቸው። ሌሎቹ ደግሞ፤ የተጀመረው ለውጥ እንዲቀጥል ስለሚፈልጉና ለውጡ ይነጋነጋል ብለው ስለሚፈሩ፤ ሁሉን ነገር ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እንተውላቸው ባዮች ናቸው። የመጀመሪያዎቹን መነጋገር ያለብን አይመስለኝም። እናም አልፈዋለሁ። ሁለተኛዎቹን በሚመለከት፤ ያንድ ሰው ድካም ይበቃል ወይንስ ሁላችን የምንረባረብበት? በሚል እመልሰዋለሁ።

አንድ ብቻቸውን የሚደክሙት ጠቅላይ ሚኒስትር፤ ባሁኑ ጊዜ፤ ዙሪያቸውን ከከበቡት መካከል ነባር የሕዝቡ ጠላቶች አሉ። በግለሰብ ደረጃ እሳቸውን፤ ያን ካልቻሉ ደግሞ ሥራቸውን ለማደናቀፍ ወደኋላ የማይል ኃይል አለ ማለት ነው። መርሳት የሌለብን፤ ሕይወታቸውን ለማጥፋት ሞክረዋል። እሳቸውን ማጣት ከባድ ውድቀት ነው። ነገር ግን፤ በሳቸው ተማምኖ መጋለብ ኃላፊነት የጎደለው ሂደት ነው። እሳቸውን መንገር ያለብን፤ አሁን ሀገራችን የምትፈልገው፤ የሽግግር መንግሥት ተቋቁሞ፤ ውስብስቡን የሀገራችን ችግር፤ ባገር አቀፍ ጥሪ መፍታት ነው። እንዴት ሊቋቋም ይችላል? እንዲህ አይሆንም ወይ? ያ ችግር አያስኬድም? የመሳሰሉ ምክያቶችን መደርደር ይቻላል። ነገር ግን ከዚህ የቀለለ ሌላ መንገድ የለም። ስለ ሽግግር መንግሥት አቋቋም፤ በሚቀጥለው ጽሑፌ በሠፊው እሄድበታለሁ። ወይንም ሌሎች ሊያቀርቡ ይችላሉ። ዋናው ግን፤ ካለንበት አዘቅት መውጣት የምንችለው፤ ካሁኑ ቦታችን ወደምንፈልገው ቦታ ለመድረስ፤ የሽግግር መንግሥት ግዴታ ነው። ምን ትላላችሁ?

ከታላቅ አክብሮት ጋር
አንዱዓለም ተፈራ

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

የቀን ጅቦችና መሰሪ ተግባራቸው፤

የቀን ጅቦችና መሰሪ ተግባራቸው፤

አንዱዓለም ተፈራ

ሰኞ፤ ሐምሌ ፱ ቀን፣ ፳፻፲ ዓመተ ምህረት

በዐማራውና በኦሮሞው ኅብረት ደማቸው የፈላና፤ እየተካሄደ ያለውን ለውጥ ለማደናቀፍ የሚንቀሳቀሱ የቀን ጅቦች፤ በዐማራውና በኦሮሞው መካከል ጠብ ለመጫር ያለ የሌለ ጉልበታቸውን እያፈሰሱ ነው። ከዚህ መካከል አንዱ ዘዴያቸው፤ በታሪክ እኒህን ሁለቱ ታላላቅ የኢትዮጵያ አካሎች ማጣላት ነው። ዐማራ ኢትዮጵያን በሚመለከት፤ ሰንደቋን አንግቦ የኖረ ሕዝብ ነው። ኦሮሞም ሀገር ገንቢና ባለቤትም ነው። በሁለቱም ወገን ገዥዎችና ተገዥዎች ነበሩባቸው። በኢትዮጵያ ስም የገዙት ከሁለቱም ብቻ ሳይሆን ከሌሎችም የተወለዱ ነበሩ።

እኒህ የቀን ጅቦች፤ ኦሮሞዎችን አሳንሰው፤ ተገዥ ብቻ፣ ዐማራው ገዥ ብቻ፣ በማድረግ፤ አንዱ ሌላውን እንዲያጠፋና የዘለዓለም ጠበኞች እንጂ፤ ሊስማሙ የማይችሉ አድርገው እየሳሉ ነው። ታሪኩ ግን ዐማሮችና ኦሮሞዎች፤ ኢትዮጵያዊ ሆነው በነበሩት ነገሥታት፤ ነገሥታቱ በነበራቸው ዕውቀትና ችሎታ፤ ሀገራችንን ጠብቀው ያቆዩ ናቸው። ይሄን ደግሞ የሌለ ታሪክ በመፍጠርና የውሽት ስዕል በመለጠፍ ተያይዘውታል። አክራሪ ኦሮሞ መስለው፤ የኦሮሞን ወጣት በጥላቻ ለመመረዝ ያደረጉትን ላሳያችሁ።

ይህ የምታዩት ፎቶ፤ አንዱ የቀን ጅብ፤ የኦሮሞ ወጣቶችን በዐማራ ጥላቻ ለመሙላት የለጠፈው ነው።

One

ይህ የውሸት ፎቶ ነው። ይሄ ፎቶ፤ ከመጀመሪያው ፎቶ ላይ፤ የአፄ ሚኒልክን የፊት ገጥ ቀዶ በማስቀመጥ፤ ለማወናበድ የተደረገ ነው። የመጀመሪያው ፎቶ ይሄውላችሁ።

Two

ልቀጥል። ይሄው ሁለተኛ ፎቶ፤

Three

ይሄኛውን ደግሞ በአፄ ኃይለ ሥላሴ ፎቶ ተክተው ለጥፈውታል።

ስድስት

ሌሎችም እንዳሉ ሁላችሁ ታውቃላችሁ። ይሄን ለምን ያደርጋሉ? የሁለቱ ወገኖች መተባበር፤ የትግሬዎች ገዥዎችን ኦድሜ ስላሳጠረ፤ በሀገር ውስጥ ሰላም እንዳይኖርና ብጥብጥ ተፈጥሮ፤ ቢቻሉ በቦታቸው ሊመለሱ፤ ካልቻሉ ደግሞ ሀገር ሰላም እንዳያገኝ ነው። ምን ትላላችሁ?

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

ግልጽ ደብዳቤ

ግልጽ ደብዳቤ

አንዱዓለም ተፈራ

ማክሰኞ፣ ሰኔ ፲ ፱ ቀን ፳ ፻ ፲ ዓመተ ምህረት

አሁን የሀገራችን የፖለቲካ ሂደት ከመቅጽበት እየተለዋወጠ በምናይበት ሀቅ፤ እየተካሄደ ያለውን ለውጥ የምንፈልግ ሁላችን፤ ከለውጡ ጠላቶች ይልቅ የለውጡ ወዳጆችን ማብዛት፤ ይሄ ይደረግ፣ ያ ይጨመር እያልን ሌሎች የኛን ፍላጎት እንዲያሟሉልን ከመሻት ይልቅ ራሳችን ምን ልናደርግ እንደሚገባን አውቀን ከለውጡ ጎን መሰለፍ ይገባናል።

ውድ ውጪሰው ኢትዮጵያዊ ታጋይ፤

በአሁኑ ሰዓት ግልጽ ደብዳቤ መጻፉ ቀላሉ ነገር ነው። በተለይ የበለጠ ቀላል የሚሆነው ደግሞ፤ ለጠቅላይ ሚንስትር አብይ አሕመድ፤ ይሄን አድርግ! ያንን አድርግ! ብሎ ትዕዛዝ ማስተላለፉ ነው። እኔ ግን ያ አይደለም ዓላማዬ።

ውድ የውጪሰው ኢትዮጵያዊ ታጋዮች፤ በያለንበት፤

አሁን የኛ ዋናው የትኩረታችን ማዕከል መሆን የሚገባው፤ እየተካሄደ ያለው ለውጥ ነው። ቀጥሎ ደግሞ፤ ቀላሉን መንገድ በመምረጥ፤ በኮምፒውተራችን መስኮት ፊት ተቀምጠን፤ ጣቶቻችንን በሆሄያት ቁልፉ ላይ ቀስረን ወይንም የመነጋገሪያ እጁን ጨብጠን፤ እከሌ ይሄን ይሥራ! እከሌ ደግሞ ያንን ያድርግ! ማለታችን ሳይሆን፤ “እኔ ይሄን የለውጥ ሂደት ምን ባደርግ እረዳዋለሁ!” ብለን ራሳችንን መጠየቅ ነው።

የሀገራችን የፖለቲካ እውነታ በጣም፤ እንደደረሰው ጥፋትና በፖለቲካው መድረክ እንደምንሳተፈው ብዛት፤ የተወሳሰበና ጥልቀት ያለው ነው። ማንም አንድ ግለሰብ፣ አንድ ቡድን፣ አንድ አስተሳሰብ በባለቤትነት በቀላሉ ሊፈታው የሚችለው አይደለም። እናም አሁን የስብስብ ጥረት፣ የስብስብ አመለካከት፣ የስብስብ የፈጥእራ ችሎት ነው ሀገራችንን ወደፊት እንድትሄድ ሊረዳ የሚችለው። ይሄን መሠረት አድርገን፤ ትብብሩንና ውአድአፊት መሄዱን ልናቃና እንችላለን።

በርግጥ በራሳች፤ በግለሰብና በወገናችን በስብስብ ላይ የተፈጸመውን በድል ልዘርዝር ለምንል ውጪሰው ኢትዮጵያዊያን፤ ባለፉት ሰላሳና ሃምሳ ዓመታት የደረሱት በደሎች፤ ብዛታቸውና ጥልቀታቸው የትዬለሌ ነው። በዚያ ላይ ብናተኩር፤ ሌላ መሥራት አንችልም። አዎ! መታረምና መፍትሔ ሊሠጣቸው የሚገባቸው ጉዳዮች አሉ። እንያን እንዳልነበሩ አድርጎ ማለፍ አይቻልም። ነገር ግን፤ አሁን ያለንበትን መሬት ማጠንከሩ ደግሞ ይቀድማል።

እናም ውጪሰው ኢትዮጵያዊያን፤ ሚናችንን እንለይ። በራሳችን በያንዳንዳችን አስተዋፅዖ ላይ እናተኩር። ተሰባስበን ልናደርግ የምንችለውን እንጣር። ርስ በርሳችን እንነጋገር። የኔ መፍትሔ ነው ወሳኙ ከሚል እብሪት እንውጣ። አክራሪ አቋም ወስዶ፤ “ያ ካልሆነ እታነቃለሁ!” ማለቱ አያዋጣም። ከፍተኛውን መስዋዕትነት እየከፈለ፤ አሁን ላለንበት የፖለቲካ ሁኔታ ያደረሰውና የትግሉ ባለቤት፤ ሀገር ውስጥ ያለው ኢትዮጵያዊ ነው። ከፍተኛ አስተዋፅዖ ማድረግ እንችላለን፤ ካወቅንበት! በአንጻሩ ደግሞ የችግሩ አካል መሆን እንችላለን፤ ካላወቅንበት! እስካሁን በትግሉ ዙሪያ ለነበርነውም ሆነ አዲስ ተሳታፊዎች፤ ጌዜው አሁን ነው። መወያየት ለሚፈልግ፤ eske.meche@yahoo.com

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

ለጠቅላይ ሚንስትር ዓብይ አሕመድ ያለኝ ድጋፍና እያየን ያለነው የለውጥ ሂደት ከአንድ ዐማራ ዕይታ አንጻር

ለጠቅላይ ሚንስትር ዓብይ አሕመድ ያለኝ ድጋፍና እያየን ያለነው የለውጥ ሂደት ከአንድ ዐማራ ዕይታ አንጻር
አንዱዓለም ተፈራ
ሰኔ ፲ ፯ ቀን እሁድ ፳ ፻ ፲ ዓመተ ምህረት ( 6/24/2018 )

ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አሕመድ፤ በጣም በአጭር ጊዜ ውስጥ፤ ከፍተኛ የሆነ የተስፋ በር ከፍተዋል። ይህን እያንዳንዳችን ኢትዮጵያዊያን በያለንበት ልንደግፈው የሚገባ ሂደት ነው። ይህ ነው ኢትዮጵያዊነትና የኢትዮጵያ መሪ መሆን! መቼም ላለፉት ሰላሳ ለሚጠጉ ዓመታት የደረሱት ግፍና በደሎች፤ ባንድ ቀን ጀምበር ሊስተካከሉ አይችሉም። ቁም ነገሩ ስህትቶቹ መተግበራቸውን ማመኑና፣ እኒህ ሊስተካከሉ እንደሚገባቸው መቀበሉ ላይ ነው። ጠቅላይ ሚንስትር አብይ ይሄኑ አጥብቀው ተናግረዋል። በዚህ በጣም ደስ ብሎኛል።

እንግዲህ፤ ልንዘነጋው የማንችል አንድ ሀቅ አለ። ይህ የትግሬዎቹ ነፃ አውጪ መንግሥት፤ ኢትዮጵያዊነት ራሱን ችሎ የሚገኝ ምንነት እንዳልሆነ አስምሮ፤ ኢትዮጵያዊነትን አስጥሎ፤ ዐማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ፣ ሶማሌ፣ ደቡብ፣ አፋር፣ አኙዋክ የፖለቲካ ማንነታችን መግለጫ እንዲሆን፤ በመመሪያም ሆነ በተግባር፤ ሰላሳ ለሚጠጉ ዓመታት በደረቁ ሲግተን ኖሯል። እናም በዘር ማጽዳት ደረጃ በዐማራው ላይ በደረሰው በደል፤ ተገደው ዐማራነታቸው የፖለቲካ ማንነት መለያ ካደረጉት ሌላ፤ ወደን የፖለቲካ ዐማራ የሆን ጥቂቶች አይደለንም። አሁን የሽግግር ሂደት ማድረግ እንጂ፤ የደረሰው በድል ባለበት እውነታ፤ ባንድ ዝልያ የነበርንበትን ጥለን፤ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብለን ልናጨበጭብ አንችልም። ዐማራ ኢትዮጵያዊነቱ ጥያቄ ውስጥ አይገባም። በልቡም ሆነ ባነገተው ሰንደቅ ዓላማ የሚዘክረው ኢትዮጵያን ነው።

በሀገራችን ነግሦ፤ ዐማራው ከምድረ ኢትዮጵያ እንዲጠፋ ሌት ተቀን ሲሠራ የነበረው፤ የትግሬዎች ነፃ አውጪ መንግሥት፤ ከፍተኛውን መስዎዕትነት በከፈለው በኢትዮጵያ ሕዝብ ያልታከተ ንቅናቄ ቀኑ መሽቶበታል። ይህ ደግሞ ከግቡ የሚደርሰው፤ ለዚህ ላደርሰው ግፉ መሠረት የሆነው፤ የዘረኛው መንግሥት የፖለቲካ ፍልስፍናና የአስተዳደር መመሪያው ሲቀበር ነው። ከዚያ በፊት ምንም ቢደረግ ምንም፤ ይህ ፍልስፍናና መመሪያ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ምሕዳር ላይ እስካለ ድረስ፤ የነበርንበት ተመልሶ የማይመጣበት ማረጋገጫ አይኖረንም። ለውጡ ለውጥ የሚሆነው፤ ተመልሶ እንዳይመጣ፤ መሠረቱ ሲፈርስና ማረጋገጫ ልጓም ሲኖረው ነው።

በርግጥ ጠቅላይ ሚንስትር አብይ መሐመድ የያዙት አቅጣጫ፤ ለመላ ኢትዮጵያዊያን ተስፋ የሚሠጥ ነው። መደገፍ አለባቸው። ለዐማራው፤ ወደፊት ለመሄድ፤ መሠረታዊ ከሆነው የዐማራው በቀጥታ በሀገሪቱ ሁለንተና ክንውን፤ ተሳታፊ ከመሆኑ በተጨማሪ፤ በግልጽ የተከናወኑ ግድያዎች፣ መፈናቀሎች፣ መታሰሮች፣ መሳደዶች፣ የመሬት ነጠቃዎች፣ የታሪክ ማጉደፎች፣ እና ባጠቃላይም የስብዕና በደሎች፣ መልስ ማግኘት አለባቸው። ለደረሰው ግፍ የጠቅላይ ሚንስትር አብይ መንግሥት ተጠያቂ አይደለም። ነገር ግን በዚሁ መንግሥት አሁን በአዲሱ ሂደት ተኮፍሰው ያሉና፤ በፊት ይሄን አስከፊ ድርጊት የፈጸሙ ስላሉ፤ ከኒህ ጋር አብሮ መሄድ አይቻልም። እኒህ ተጠያቂዎች ናቸው።

ይሄን ለመተግበር ደግሞ፤ አሁን ሀገራችን ውስጥ ባለው የፖለቲካ ሀቅ፤ ዐማራው ራሱን አደራጅቶ ጠይቂና ፈጻሚ መሆን አለበት። ያለው መንግሥት ሊሄድ የሚችለውን ርቀትና ሊቆም የሚችልበትን መስመር ለይተን ማወቅ ይኖርብናል። ዋናው ቁም ነገር ግን፤ የዐማራውን ፍላጎት ሊያሟላ የሚችለው፤ ዐማራው ራሱ መሆኑን ከልባችን ማስገባቱ ላይ ነው።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

አፄ ሱስንዮስን ማነው ማንነት የሚለግሳቸው?

አፄ ሱስንዮስን ማነው ማንነት የሚለግሳቸው?
አንዱዓለም ተፈራ – የእስከመቼ አዘጋጅ
ረቡ፣ ሚያዝያ ፬ ቀን ፳ ፻ ፱ ዓመተ ምህረት

የነበረን መተረክ እንጂ፤ ጠምዝዞ በመለወጥ፤ ያልነበረ ማድረግ አይቻልም።

አሁን ላለንበት የፖለቲካ ቀውስ ተጠያቂዎቹ እኛው ያሁኖቹ ነን። አሁን ያለንበትን የፖለቲካ ሀቅ ለመቀየር፤ ኃላፊዎቹ፤ የአሁኖቹ እኛው ነን። የትናንቱ ሀቅ፤ ትናንት በነበረው ሁኔታ የተሸመቀቀ ስለሆነ፤ ያንን ተረድቶ፤ ዛሬ ያለበትን ሁኔታ እንዳለ እንዲቀጥል ማድረግ፤ የገዥዎች ጥረት ነው። ይሄንን ለመቀየር መጣር ደግሞ፤ የታጋዮች ግዴታ ነው። በዚህ ስብጥር ሂደት፤ ወደ ኋላ ተመልሶ፤ አንድም ተጠያቂነትን ለቀድሞዎቹ መሥጠት፤ አለያም ደግሞ፤ ያልነበረን እንደነበረ፤ የነበረን ደግሞ እንዳልነበረ በማድረግ፤ ወደዚያ እንዳንመለስ ዓይነት ሙገታ ሲቀርብ ይታያል። በጥቅሉ፤ ይህ ሁሉ ጥረት፤ “እኔ ምንም ኃላፊነት የለብኝም!” ብሎ፤ የቀድሞዎቹን ለሁሉም ነገር ተጠያቂ በማድረግ፤ ለማምለጥ የሚደረግ የዛሬ ግብዞች ሩጫ ነው። ታሪክን መረዳት እንጂ፤ ጠምዝዞ ለመለወጥ የሚደረግ ጥረት፤ የታጋዮች ተግባር አይደለም። እስኪ በዚህ ግባት፤ የአፄ ሱስንዮስን ማንነት እና ሌሎች ለሳቸው ሊለጥፉባቸው የሚከጅሉትን ቀለም እንመለከት።

በቅድሚያ፤ ታሪካችንን የምናገኘው በሁለት መንገድ ሰፍሮ ነው። የመጀመሪያው በግዕዝ ከተጻፉትና፤ በግለሰቦች እጅም ሆነ በደብራት ከሚገኙ የብራና ጽሑፍት ነው። ሌላው ደግሞ፤ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው፤ እኒሁኑ መጽሐፍት አገላብጠውና አስተርጉመው፤ ለራሳቸው ምርምር በሚረዳቸው መንገድ በዘገቡ የውጪ ጎብኝዎች፤ ወይንም የታሪክ ተመራማሪዎች ነው። ባንደኛውም ሆነ በሁለተኛው መንገድ የምናገኘው ታሪካችን፤ አሁን ላለነበት ሁኔታ ተጠያቂ አይደለም። ነገር ግን፤ ያንን ተረድተን፤ ያንን አውቀን፤ እኛ አሁን ያለንበት ሁኔታ የራሳችን ኃላፊነት መሆኑን ተገንዝበን፤ ትምህርት ለመውሰድ ይረዳን ዘንድ፤ በትክክል ማወቁ፤ የግድ ነው። አሁንም፤ የነበረን መተረክ እንጂ፤ ጠምዝዞ ያልነበረ ማድረግ አይቻልም።

የኢትዮጵያን የነገስታት ታሪክ በዘመናዊ መልክ ጽፈው ካገኘኋቸው ኢትዮጵያዊያን ውስጥ፤ ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ የመጀመሪያው ናቸው። ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ የጻፉት፤

ዋዜማ።

በማግስቱ የኢትዮጵያን ነገስታት

የታሪክ በዓል ለማክበር፤

የሚለው በ ፲ ፺ ፻ ፳ ፩ ዓመተ ምህረት የመጀመሪያ ዕትሙ፤ በ ፳ ፻ ፩ ዓመተ ምህረት ደግሞ፤ የልጅ ልጃቸው አቶ ሽመልስ ይልማ ያሳተሙት መጽሐፍ፤ መረጃዬ ነው።

በዚህ መጽሐፍ ገጽ ፶ ፬ የሚጀምረው ምዕራፍ ፮፤ በኢትዮጵያ የነገሡትን ነገሥታት፤ ከአፄ ይኩኖ አምላክ ( የክርስትና ስማቸው፤ ተስፋ እየሱስ )  እስከ ጎንደሩ ንጉሥ አፄ ሠርፀ ድንግል ድረስ ዝርዝራቸውን ያቀርባሉ። አፄ ይኩኖ አምላክ፤ ከዛጔ ነገሥታት ተደብቀው ይኖሩ የነበሩ፤ የቀዳማዊው የሚኒልክ ተወላጅ ናቸው። አፄ ይኩኖ አምላክ እሰከ ዛጔው ንጉሥ ነዓኩተለዓብ ድረስ በድብቅ ቆይተው፤ በኋላ በአቡነ ተክለሃይማኖት ጣልቃ ገብነት፤ የሚኒልክን ትውልድ በሥልጣን ላይ ለማውጣት ባደረጉት ጥረት፤ ተሳክቶላቸው፤ ለመንገሥ በቅተዋል። ይህን ሁሉ ሂደት፤ አሁን በዚህ ወቅት የምንገኝ ሰዎች፤ አሁን ባለን ግንዛቤ መቀበሉ ያዳግተናል። ነገር ግን፤ መረዳት ያለብን፤ የዚህ ወቅትና የኛ ወቅት የተለያየ መሆኑን ነው። የተለያየ ማለት ደግሞ፤ በግንዛቤም ጭምር ነው።

ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ በዚህ ዝርዝራቸው፤ ከአፄ ይኩኖ አምላክ በቀጥታ የሚወለዱት ፳ ፬ ኛው ንጉሥ አፄ ልብነ ድንግል ናቸው፤ ብለው አስፍረዋል። አፄ ልብነ ድንግል በነበረው የፖለቲካ ሀቅ፤ የአፋርና የሶማሌ ወገኖቻቸውን አሰባስበው በዘመቱባቸው በአህመድ ኢብን ኢብራሂም ( በተለምዶ ግራኝ መሐመድ ) ተገደው፤ ግዛታቸውን ከሸዋ ነቅለው ወደ አማራው አገር ወስደዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ ምሁር የሆኑት ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴም ይሄንኑ ታሪክ፤

A History of

Modern Ethiopia

1855 – 1991

በሚለው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዕትማቸው፤ የአፄ ይኩኖ አምላክን አነጋገስ፤ ከብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ ለየት ባለ መንገድ፤ በመቅድማቸው በገጽ ፰ እና ፱ ላይ ይሄንኑ አስፍረዋል።

ለዚህ ጽሑፍ፤ እኒሁ ሁለቱ ማስረጃዎች፤ ከሞላ ጎደል ሌሎች ያካተቱትን አጠቃለው ስለሚይዙ በቂ ናቸው። ሆኖም ግን ይሄንኑ ታሪክ ለማመሳከር፤ ሌሎች ከዚሁ ትረካ ጋር አንድነት ያላቸው ጹሑፍት መኖራቸውን ከወዲሁ እገልጻለሁ።

እዚህ ላይ አንድ ሀቅ ማስፈር እፈልጋለሁ። ምንም እንኳን አሁን በኛ ጊዜ ቦታ ባይኖረውም፤ በዚያ ወቅትም ሆነ እስከዛሬ ድረስ፤ ነገሥታት በተለያየ ሁኔታ፤ ከተለያዩ ወገኖች፤ መጋባታቸውና መዋለዳቸው ሀቅ ነው። ሆኖም ግን፤ ጋብቻ የሚፈጽሙት፤ ለነበሩበት የፖለቲካ ሁኔታ መጠቀሚያ ለመግዛት እንጂ፤ ዘራችንን ለመቀየጥ ወይንም ማንነታቸውን ለመለወጥ፤ ስሌት አግብተው አልነበረም። እናም ከሌላ ወገን ሲያገቡ፤ ያ ወገን በግዛታቸው ተጠቃሎ እንዲገብርላቸው ነበር። እናም፤ አብዛኛው ነገሥታት፤ ከሌላ ወገን ሚስቶችን በማምጣት ተጋብተዋል። በዚህም ግዛታቸውን አስፍተዋል። ጠብ አብርደዋል። ተቀናቃኞቻቸውን አምክነዋል። የንግሥና የትውልድ ቆጠራቸውን በነገሡት አባቶቻቸው ስበዋል። በዚህም፤ የአብዛኛዎቻቸውን እናቶች ካለማወቃችን ባሻገር፤ የእናቶቻቸው ትውልድ፤ ባፈ ታሪክ በተለወሰ ልቁጥ ተሸክፏል።

ወደ አፄ ልብነ ድንግል ስንመለስ፤ አጠቃላይ የንግሥና ዘመናቸው፤ ከ ፲ ፭ ፻ እስከ ፲ ፭ ፻ ፴ ድረስ ለሰላሳ ዓመት ሲሆን፤ ልጃቸው አፄ ገላውዲዎስ፥ ፲ ፱ ዓመት ነግሠዋል። በወቅቱ በነበረው የፖለቲካ ግጭት፤ ቱርኮች አህመድ ኢብን ኢብራሂምን ሲረዱ፤ ፖርቹጋሎች ደግሞ ንጉሡን ይረዱ ነበርና፤ አፄ ገላውዲዎስን፤ ፖርቹጋሎች አወናብደው፤ የእኩልነት ግዛት ስጠን ሲሏቸው፤ ከፈለጋችሁ እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ መኖር ትችላላችሁ። ከዚህ ሌላ ግን አባቴ ምንም ውለታ አልገባላችሁም፤ በማለት፤ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ፤ አረንጓዴ፣ ብጫ፣ ቀዩ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ብቻ እንጂ፤ የፖርቹጋል መንግሥት ሰንደቅ ዓላማ፤ በኢትዮጵያ መሬት እንዳይያዝ ብለው አዘዋቸዋል። የአፄ ገላውዲዎስ ልጅ፤ አፄ ሚናስ ናቸው። አፄ ሚናስ፤ ወደ ሸዋ ከመመለስ ይልቅ፤ በጎንደር እንደነገሡ ቀሩ። ልጃቸው አፄ ሠርጸ ድንግል መንግሥታቸውን በጎንደር ስላደረጉ፤ የጎንደር መንግሥት በሳቸው እንደተጀመረ ይነገራል።

እንግዲህ ወደ ጽሑፌ ርዕስ ስመለሰ፤ አፄ ሠርፀ ድንግል አፄ ያዕቆብን ይወልዳሉ። አፄ ያዕቆብ ደግሞ አፄ ሱስንዮስን ይወልዳሉ። አፄ ሱስንዮስ የዝነኛው የአፄ ፋሲል አባት ናቸው። ከአራት አምስት ወራት በፊት ከዶከተር ኃይሌ ላሬቦ ጋር ባደረግሁት ልውውጥ፤ የዚህ የአፄ ሱስንዮስን የትውልድ ጉዳይ አንስተን ነበር። እሳቸው፤

እንግዴህ ስለአፄው ከሆነ፣ እኔ እንደማውቀው እሳቸው ማለትም አፄው ( አፄ ሱስንዮስን ማለታቸው ነው – የኔ ) ራሳቸው በቀጥታ ከደቡብ ብሔረሰብ አይወለዱም። ከደቡብ ብሔረ ሰብ ዝምድናቸው በምንዝላታቸው ማለትም በዐምስተኛ አባታቸው ሊሆን ይችላል። የአፄ ናዖድ እናት ወይንም የአፄ በዕደማርያም ባለቤት ንግሥት ሮምኔ [ሮማነወርቅ] ትውልዳቸው ከአዳል ወይንም ከሐዲያ ነው የሚል ዜና አለ። ግን ርግጠኝነቱ ያጠያይቃል።”  ( መመንዘል = ማክበድ  – የኔ )

ብለውኛል።

እዚህ ላይ፤  አፄ ናዖድ à አፄ ልብነ ድንግልን à አፄ ገላውዲዎስን à አፄ ሚናስን à አፄ ሠርፀ ድንግልን à አፄ ያዕቆብን à አፄ ዘድንግልን è ከዚህ በኋላ አፄ ሱስንዮስ የተከተሉ መሆናቸውን ላሰምርበት እፈልጋለሁ። ( አምስተኛ ሳይሆን በቀጥታ ከቆጠርነው ሰባተኛ መሆኑ ነው። በተጨማሪ፤ ከአፄ በዕደማርያም የተከተሉት አፄ እስክንድር ሲሆኑ፣ ከአፄ እስከንድር ደግሞ አፄ አምደ ጽዮን ተከትለዋል። አፄ ናዖድ ከዚያ ነው የቀጠሉት። ነገር ግን፤ ይሄን ብልም፤ የወንድማማቾች መከታተል ሊኖር ስለሚችል፤ ዝርዝሩን ላለማንዛዛት ብየ ስለተውኩት ነው፤ ቆጠራው ሊለያይ ይችላል። ) አፄ ሱስንዮስ፤ በንግሠታቸው፤ ፍጹም አማራ ናቸው ማለት ነው።

መረጃ ይሆን ዘንድ፤ የአፄ ሱስንዮስን ከኦሮሞነት ጋር የመያያዝ ግንዛቤን ሊያስከትል የሚችል ሁኔታን ግልጽ ላድርግ። አፄ ሱስንዮስ፤ አቤቱ በተባሉበት በወጣትነታቸው ወቅት፤ ከቤተመንግሥት ሸሽተው፤ ወደ ኦሮሞዎች ዘንድ ሄደው በዚያ አድገዋል። እናም ለመጎልበት፤ የአማራና የኦሮሞ ጦር አሰባስበዋል። በኋላ ደል ካደረጉና፤ ከቤተክህነት እየራቁ ሲሄዱ፤ የአማራ ባላባቶችንና የቤተክህነትን ጉልበት ለማዳከም፤ ዕውቅ የሆኑ የኦሮሞ ደጋፊዎቻቸውን ከደቡብ አምጥተው፤ በጎጃም፣ በቤጌምድርና በመላው አማራ ግዛታቸው አስፍረዋል። ያ ብቻ ሳይሆን፤ መሬትና ጥሪት አድለዋቸዋል። ሹመትም ሠጥተዋቸዋል። የወሰዱት መሬት፤ ከቤተክህነት መሬትም ጭመር ነበር። ይህ የቤተክህነት ሰዎችን ቅሬታ አብዝቶባቸዋል። በርግጥ ከፖርቹጋሎች ጋር የነበራቸው ግንኙነትና መኮትለካቸውን ተከትሎ፤ ደንቢያ ላይ የራሳቸውን ቤተክርስትያን እንዲያቋቁሙ ቦታ ሠጥተው፤ በደንቀዝ ቤተ መንግሥታቸው የካቶሊኩን ፖርቹጋላዊ ቄስ፤ ፔሮ ፓይዝን ማስፈራቸው፤ ለተከተለው ውድቀት ዳርጓቸዋል።

አንድ ነገር ግልጽ ማድረግ እፈልጋለሁ። አፄ ሱስንዮስ ያገቧቸው ወልደ ሰዓላ ( ሌላም የንግሥና ስማቸው ሥልጣን ሰገድ ) የሚባሉ ባላባት ናቸው። እሳቸው ወደ ጎንደር የመጡት ከመርሃቤቴ ነው። በጎንደር እነ ፋሲልን፣ ገላውዲዎስን፣ ወለተ ገብርዔልን እና ሌሎችንም ወልደው፤ የሃይማኖት ንትርኩ ስላልጣማቸው፤ በ፲፮፻፲ ወደ ቆማ ወረዱ። ከዚያ የቆማ ፋሲለደስን መሥርተው፤ በዚያው በ፲፮፻፶፫ ዓመተ ምህረት አድፈው፤ እዚያው አስከሬናቸው አርፏል። አፈ ታሪኩ፤ እኒህን ንግሥተ ነገሥት ሥልጣን ሰገድን፤ የወለጋ ኦሮሞ ባላባት ዘር አለባቸው ይላል። እንግዲህ ይህ አፈ ታሪክ ነው። ነገሥታት የንግሥና ትውልድ ሐረጋቸውን የሚቆጥሩት በወንድ ትውልዳቸው ነው። እናም በወቅቱ በነበረው ሂሳብ፤ አፈ ታሪክነቱ እንዳለ ሆኖ፤ አፄ ፋሲልን ኦሮም አያደጋቸውም።

እንግዲህ አፄ ሱስንዮስ፤ ከአማራነታቸው በስተቀር፤ በጽሑፍ የሰፈረ ምንም ማስረጃ የለም ማለት ነው። ታዲያ ማነው ለሳቸው የማንነት ምልክት ሊሠጣቸው የተነሳ? ማምለጫ ይሆናል በማለት፤ “ይባላል!” “ሌሎች ያላሉ!” ወይንም “የሚባል ነገር አለ!” በማለት፤ ጥርጣሬን ሆን ብሎ ለማስገባት የሚደረግ ጥረት አለ። እዚህ ላይ ሁለት ነገሮችን እንድናስተውል እፈልጋለሁ። የመጀመሪያው፤ ወሬው በማን ተናፈሰ የሚለው ሲሆን? ሁለተኛው ደግሞ፤ ወሬው ለምን ተናፈሰ የሚለው ነው።

ይህ እንዳለ ሆኖ፤ አሁን ወሬው ለምን ተናፈሰ? ይህ ከበጎም በጎ ካልሆነ ዓላማ ሊራገብ ይችላል። በጎ የምለው፤ በቅንነት ነገሥታቱ ሁሉ የኢትዮጵያ ነበሩና፤ በመካከላችን፤ ገዥ ብሔርና ተገዥ ብሔር የሚባል የለም ከሚል ነው፤ ብዬ እገምታለሁ። ነገሮችን በቅን መንፈስ ማየት እፈልጋለሁ። ይህ ካልሆነ፤ ትርጉሙ ለኔ በጠጠረ መንገድ፤ ነገሥታትን ለማሳነስ፣ ታሪክን ለመጠምዘዝና፤ አገር ለማናጋት ይሆናል እላለሁ።

ወሬው በማን ተናፈሰ? ይህም ቢሆን ሁለት ምንጮች አሉት ይመስለኛል። የመጀመሪያው፤ እባካችሁ አንድ ነን። የቀድሞዎቹ ይሄን የኛን ንትርክ አላገናዘቡትም። እናንተ ዝም ብላችሁ ስላሁኑ ተጨነቁ። ከሚል ከቅንነት የሚያስቡ ግለሰቦች ናቸው እላለሁ። ሌላው ምንጭ ግን፤ አማራውን ታሪክና እMነት ለማሣጣትና ለተንኮል ነው እላለሁ። በዚህም ሆነ በዚያ መንገድ፤ ይህ አላስፈላጊ ትረካ ባሁኑ ሰዓት ወደ አደባባይ መውጣቱ፤ ክፍተትን ለማብዛት ካልሆነ በስተቀር፤ በትግሉ ዘንድ አስተዋፅዖ የለውም። አሁን አማራው የሕልውና ጥያቄ አፋጦት፤ ማንነቱን፣ ታሪኩን፣ ቋንቋውን፣ ባህሉን ለማስመርና ሕልውናውን ለመጠበቅ በሚያደርገው ትግል፤ አዘናጊ ነው እላለሁ።

ይህ ታሪክ ለኔ ልዩ ትርጉም አለው። ስለራሴም የሚናገር ክፍል ስላለበት፤ በቀጥታ ከልጅነት ጀምሮ ያጠናሁትን የጠየቀ ጉዳይ ነው። እናም የትም ቦታ ማስረጃ አቅርቤ ልነጋገርበት የምችለውና የሚገባ ግዳጄ ነው።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ

ሥርዓት ለመለወጥ የሚደረግ የፖለቲካ ትግል፤ ወይንስ የተበታተነ ተቃውሞ?

ሥርዓት ለመለወጥ የሚደረግ የፖለቲካ ትግል፤ ወይንስ የተበታተነ ተቃውሞ?
አንዱዓለም ተፈራ – የእስከመቼ አዘጋጅ
አርብ፣ መጋቢት ፳ ፱ ቀን ፳ ፻ ፱ ዓመተ ምህረት

የያዝነውን እናጢን!

ምን እያደረግን ነው?

የትግሬዎቹ ገዢ ቡድን በሚያደርገው የዕለት ተዕለት አውዳሚ ተግባሩ በመቆጣት፤ ለተቃውሞ መነሳትና፤ ይህን አካል በተግባሩ ወንጅሎ፤ በደሎቹን መዘርዘሩ አንድ ነገር ነው። ይህ ተቃውሞ ነው። በመቃወምና ይህ መደረግ የለበትም ብሎ በመጮህ፤ የተወሰነ ግብን ማስገኘት ይቻላል። ተግባሩ ግን ይቀጥላል። ቢበዛ ቢበዛ፤ በተግባሩ ሂደት ላይ ትንሽ ማስተካከያ ማስከተል ይቻላል። ከዚያ በተረፈ ግን፤ ይህ በመፈጸም ያለ በደል፤ በድጋሚ እንዳይከሰት የሚያቆመው ነገር የለም። ይሄን በማድረግ የሚረካ ሊኖር ይችላል። እንደገና፤ ይህ ተቃውሞ ነው።

በታቃራኒው ደግሞ፤ የተፈጸሙትና በመፈጸም ላይ ያሉት በደሎች፤ “መደረግ የለባቸውም!” ብሎ መነሳት ብቻ ሳይሆን፤ “የዚህ ሁሉ ምንጩ፤ አንድ አካል ነው። ይህ አካል መንግሥታዊ ሥልጣኑን ባንድ መንገድ ወይንም በሌላ፤ በጁ ጨብጧል። ይህ አካል ይህን በደል መፈጸሙ፤ ስነ ፍጥረቱ ነው። ከዚያ የተለየ ሌላ ሊያደርግ አይችልም። እናም ይህ አካል መወገድ አለበት!” ማለትና፤ ይህን አካል የሕዝቡ በሆነ አካል ለመተካት መነሳት፤ ሌላ ነው። ይህ ሥርዓትን ለመለወጥ የሚደረግ፤ የፖለቲካ ትግል ነው።

በኒህ ሁለቱ መካከል ያለውን መሠረታዊ ልዩነት ሁላችን እናውቃለን። እስኪ ከዚህ አንጻር የያዝነውን ሂደት፤ ምን እያደረግን እንደሆነ እንመለክት። የእስልምና ተከታዮች ተቃውሞ፣ የአኝዋክን መጨፍጨፍ ተቃውሞ፣ በጉራፈርዳ የአማራዎችን መፈናቀል ተቃውሞ፣ ለሱዳን ደንበር ተቆርሶ መሠጠቱን ተቃውሞ፣ የሀገሪቱን ወደብ አልባ መሆን ተቃውሞ፣ የወልቃይትን አላግባብ ወደ ትግራይ መጠቅለል ተቃውሞ፣ የኦሮሞዎችን በገፍ ወደ እስር ቤት መነዳት ተቃውሞ፣ የኦጋዴኖችን ሆን ብሎ ማስራብ ተቃውሞ፣ የሠራተኞች፣ የመምሀራን፣ የተማሪዎች፣ የሴቶችና የጋዜጠኞች ማኅበራትን መፍረስና የመሪዎቹን መታሰርና መሰደድ ተቃውሞ፣ የወጣቶችን በገፍ መጨፍጨፍ ተቃውሞ፣ መምህራን ያለአግባበ ከሥራቸው ስለተባረሩ ተቃውሞ፣ የሕዝብ ድምጽ በመሰረቁ ተቃውሞ፣ ሌሎችን በማራቆት የትግሬዎችን በተለይ ተጠቃሚነት ተቃውሞ፣ የአማራዎችን በፖለቲካ ፍልስፍናና በመንግስታዊ አስተዳደር፤ አልፎ ተርፎም በዘር አጥፊ ሂደት መጠቃት ተቃውሞ፣ የአማራዎች በገደል መወርወር፣ በየቦታው መገደልና መታሰር፣ እንደ እንሰሳት ሥጋቸው ታርዶ መበላት ተቃውሞ፣ መንግሥታዊ አካላት ከሌሎች ኢትዮጵያዊያን ጸድተው፤ በትግሬዎች ብቻ በመሞላት፤ ትግሬዎችና የትግራይ ክልል፤ ከተመጣጣኝ ተገቢ ድርሻቸው በላይ፤ የሀገሪቱን ንብረትና የመበልጸግ ዕድል ማግኘት ተቃውሞ፤ . . . መዘርዘሩ የሚያቆም አይደለም። ይህን ማንም ኢትዮጵያዊ ሁሉ ያውቀዋል። ታዲያ ይሄ ሁሉ ተቃውሞ ምን ሊያስከትል ይችላል? ይሄን እያደረግን መሆናችንን ማንም የሚክደው አይደለም። ተቃውሞ ነው የያዝነው ብል፤ ተሳስተሃል የሚለኝ ካለ፤ ልማር ዝግጁ ነኝ።

“ታዲያ ይሄ አይሰራም ካልክ፤ አንተ ሥርዓት ለመለወጥ የሚደረግ የፖለቲካ ትግል ስትል፤ ምን ማለትህ ነው?”  የሚል ጠያቂ አይጠፋም። ተገቢ ነው። ትክክለኛ ጥያቄም ነው። መልስ መሥጠትም ግዴታዬ ነው።

ከላይ የተዘረዘሩትን ሁሉ የፈጸመው አንድ የትግሬዎች ገዥ ቡድን ነው። ይህ የትግሬዎች ገዥ ቡድን፤ ከላይ የተዘረዘሩትን በደሎች ሲፈጽም፤ እያንዳንዳቸውን በተናጠልና የማይገናኙ አድርጎ አይደለም። ስለዚህ፤ መገንዘብ የሚያስፈልገው፤ እኒህ ድርጊቶች የአንድ አጥፊ ቡድን፤ መሠረታዊ እምነቶችና፤ የተለያየ ግብ ያላቸው፤ ነገር ግን የተሳሰሩና ወደ አንድ አቅጣጫ የሚያመሩ የፖለቲካ እርምጃዎች ናቸው። አንደኛውን ከሌላኛው የሚያስተሳስረው ገመዱ፤ ሌሎችን በማውደም፣ ታሪክን በመጠምዘዝ፣ አንድ አዲስ ሕልውና ለማምጣት የተሴረ መሆኑና፤ ይህን ሁሉ ደግሞ የትግሬዎቹ ገዥ ክፍል የፈጸማቸው መሆናቸው ነው። አንድ ኅብረተሰብ፤ በሂደት ይቀየራል፤ ያድጋል። ማደጉም ተገቢ ነው። የሰው ልጅ የሥልጣኔ ግስጋሴ ግድ የሚለው፤ የነበረውን እየፈተሸ፣ በሂደቱ አዲስ ግኝቶችን እያካተተ፤ ለውጦችን እያስከተለ፤ ያለፈው ትውልድ ለወደፊቱ ትውልድ ማስረከቡን ነው። ባለበት የቆመ ኅብረተሰብ፤ የሕልውና ጊዜው ውስን ነው።

ይህ ገዢ ቡድን፤ አሁንም ራሱን፤ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር ብሎ ይጠራል። ነገር ግን፤ ራሳቸው ትግሬዎች ገዥ በሆኑበት አገር፤ ትግሬዎቹን ከማንና ከምን ነው ነፃ የሚያወጣቸው? አንድ በሉ። ሕግ ማለት የትግሬዎቹ ገዥዎች የሚፈልጉት ማለት በሆነበት አገር፤ ሕግና ሥርዓት ፍለጋ መውጣት የዋኅነት ነው። ሁለት በሉ። ማንነትሽንም እኔ ነኝ የምነግርሽ፤ የሚል ገዥ ቡድን ባለበት አገር፤ አገር አለኝ ብሎ ማለት አይቻልም። ሶስት በሉ። የምትኖርበትን ቦታ የምሠጥህና የምነጥቅህ እኔ ነኝ ያለን ገዥ፤ ትግሬው ላልሆነ ሁሉ፤ የኔ ገዥ ነው ብሎ ማለት አይቻልም። አራት በሉ። ይሄን ሁሉ በመደመር ነው፤ አስፈላጊ የሚሆነው፤ ሥርዓትን የሚለውጥ የፖለቲካ ትግል ነው፤ የምለው።

የትግሬዎቹ ገዥ ቡድን በሥልጣን ላይ በቆየበት ሃያ አምስት ዓመታት፤ በጣም መሰረታዊ የሆኑና አስቸጋሪ ለውጦችን በኢትዮጵያ የፖለቲካ ሕይወት ላይ ጭኗል። ጊዜ በወሰዱ ቁጥር፤ እኒህ ለውጦች፤ ሥር እያበጁ ተተክለው፤ አዲሱን ትውልድ በክለው፤ በሕዝቡ ስነ ልቦና ውስጥ እየተጋገሩ፤ የወደፊቱን መንገድ ውስብስብ እያደረጉት እንደሆነ ግልጽ ነው። እኒህን መቅረፉ የጊዜ ጉዳይ ነው። ላሁን ግን፤ እኒህን ሀቅ ብሎ ወስዶ፤ በኒህ ዙርያ፤ የፖለቲካ ትግሉን ማድረጉ፤ የኛ ኃላፊነት ነው። እንግዲህ ዛሬ ለተያዘው የትግላችን መነሻ የሚሆነው፤ የትናንት ወይንም የነገ የፖለቲካ ሀቅ አይደለም። አሁን ያለንበት የዛሬው የፖለቲካ ሀቅ ነው ገዥያችን። ትግሉ የዛሬ፤ የዛሬውን ትግል ገዥ ደግሞ፤ የዛሬው የፖለቲካ ሀቅ ነው።

እስኪ የዛሬውን የፖለቲካ ሀቅ እንመለከት።

የትግሬዎቹ ገዥ ቡድን ከጠዋቱ ሲነሳ፤ “ትግሬዎች የራሳችን መንግሥት መመሥረት አለብን!” ብሎ ነው። ይህን በተግባር ለማዋል ደግሞ፤ “አማራውን መቃብር ውስጥ ማስገባት አለብኝ!” ብሎ በመርኀ-ግብሩ አስፍሮ ነው። እንግዲህ ይህ የትግሬዎች ቡድን የተነሳው፤ በአማራው መቃብር ላይ፤ የትግሬዎችን ሪፑብሊክ ለመመሥረት ነው። አንዱ ጠፍቶ ሌላው መኖር አለበት! የሚል የፖለቲካ መርኅ አንግቶ ነው። በተግባርም ያደረገው ይሄንኑ ነው። ለአማራዎች፤ ይሄን የትግሬዎች ቡድን፤ “ተው! እሱን አታድርግብን!” ብሎ ልመና ወይንም ለዚህ አካል አቤቱታ ማቅረብ ወይንም ለክስ መነሳት፤ ጹም የማይታሰብ ነው። ስለዚህ፤ አማራዎች ራሳቸውን ከጥፋት ለማደን፤ ተደራጅተው መከላከል አለባቸው። ይሄን ማንም ሊነግራቸው፤ ወይንም አድርጉ! አታድርጉ! ብሎ ሊያዛቸው አይችልም። ይሄን ካላደረጉ፤ ራሳቸው ይጠፋሉ። የወደፊት ትውልድም አይኖራቸውም። ታሪክ ይጠይቃቸዋል!

ይህ የትግሬዎቹ ገዥ ቡድን እስካለ ድረስ፤ አማራው ሕልውናው አደጋ ላይ ነው። ከሌሎች ኢትዮጵያዊ ወንድሞቹ የተለየ የሕልውናው ኃላፊነት አለበት። ይሄን ጠቅጥቆ ሊሄድ አይችልም። ስለዚህ አማራው በአማራነቱ ብቻ ተደራጅቶ፤ ራሱን ከመጥፋት ማዳን አለበት። ይህን በማድረግ ላይ ነው። ሀገሩን አልካደም። ሰንደቅ ዓላማውን አልካደም። ነገር ግን፤ በአማራነቱ እንዲደራጅና እንዲታገል፤ ያለንበት የፖለቲካ ሀቅ ግድ ብሎታል። ስለዚህ አማራው በአሁን ሰዓት፤ ያላማራጭ፤ በአማራነቱ መደራጀት አለበት።

ሌሎችስ? የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል። ተገቢም ነው። ሌሎችም በአማራው ደረጃ አይሁን እንጂ፤ ለትግሬዎች መጠቀሚያ ሲባል፤ በተጠቂነት ላይ ያሉ ናቸው። ስለዚህ፤ እነሱም መነሳት ግዴታቸው ነው። አነሳሳቸው እንደ አማራው አይሆንም። ከአማራ ጋር ግን፤ ጎን በጎን መነሳት ይችላሉ፤ አለባቸውም። አማራው አጋራቸው ነው። እነሱም የአማራው አጋር ናቸው። አማራው እንዳልጠፋ ብሎ ሲነሳ፤ ሌሎች አማራው እንዳይጠፋ ብለው ማበሩ፤ ለነገው አንድነታቸው ይረዳቸዋል። በተቃራኒው ደግሞ፤ ከገዥው ትግሬዎች ቡድን ጋር አብረው፤ አማራውን በማጥፋት የተባበሩ አሉ። ይህ የፖለቲካ እርምጃ ነው። ተጠያቂነት አለበት። ወንጀለኛው የትግሬዎችን የበላይነት አቀንቃኙ የትግሬዎች ገዥ ቡድን፤ በርግጥ በነሱም ላይ የሚያደርገው በደል ትክክል ስላልሆነ፤ የዚህን መርዘኛ ገዥ ቡድን ማጥፋት፤ የራሳቸውም ተልዕኮ ነው። እናም መታገላቸው ለነሱም ግዴታቸው ነው።

በጎንደር ከተማ የአማራ ወጣቶች፤ እጆቻቸውን አስተሳስረው፤ “የኦሮሞ ደም የኛ ደም ነው! የእስልምና ተከታዮች መሪዎች የኛ ናቸው!” እያሉ የጮኹ ጊዜ፤ ሌሎችን የትግል አጋር አድርገው መነሳታቸውን አብሳሪ ነበር። የአንድነቱን ሰንደቅ ከማንም በላይ ከፍ አድረገው መያዛቸው ነው። በዚህ የአማራውች ትግል ምንነቱንና አቅጣጫውን መመልከት ይቻላል።

እዚህ ላይ፤ ባንድ በኩል፤ የትግሬዎችን ገዥ ቡድን የማውደም ተልዕኮ አለ። በሌላ በኩል ደግሞ ተከትሎ የሚመጣውን ሥርዓት መለየትና ማወቅ አለ። የሚከተለውን ሥርዓት አስመልክቶ፣ አማራው፤ “በደረሰብኝ የዘር ማጥፋት ሂደት፤ ተጠያቂ አለና፤ ይታሰብልኝ። ለወደፊቱም ይሄን የመሰለ እንዳይደገምብኝ፤ ማስተማመኛ እፈልጋለሁ!” ይላል። አኙዋኩ ደግሞ ተቀርRቢ ጉዳይ ይዟል። ኦሮሞውም ሆነ ኦጋዴኑ ከዚህ አይርቅም። አዎ! መገንዘብ ያለብን፤ አሁን ያለው ሀቅ ይህ መሆኑን ነው። ይሄን አደባብሰን፤ “የአንድነት ትግል ብቻ ነው ማካሄድ ያለብንና፤ በአንድነት ወደፊት እንሂድ!” ብንል፤ በመካከላችን መጠምዘዣዎችን ማበጀትና ርስ በርሳችን ሳንተማመን መጓዝ ስለሚሆን፤ የትግሬዎቹን ገዥ ቡድን ዕድሜ ከማርዘም በስተቀር፤ የምናደርገው ሌላ ፋይዳ የለም።

በዚህ በፖለቲካው ትግል፤ ሁለቱ መሠረታዊ የሆኑት ጉዳዮች በፊት ለፊት ቀርበው፤ በታጋዩ ክፍል መካከል፤ ስምምነት መገኘት አለበት። ለየብቻ የምናደርገው ግልቢያ፤ ተቃውሞ ከማቅረብ የተለየ አይደለም። በርግጥ ለየብቻ ትግሉ ለየብቻ መጥፋት እንደሆነ ማንም አይስተውም። እናም፤ ትግሉን በአንድነት ለማድረግ፤ የአንድነት መሠረቱንና ሂደቱን ከወዲሁ መነጋገርና፤ አንድ ቦታ ላይ መድረሱ፤ ቅድሚያ ቦታ ይይዛል።

አንድነት ስል፤ በሥልጣን ላይ ያለውን የትግሬዎች ገዥ ቡድን ለማስወገድና፤ ከድሉ በኋላ በሚመሠረተው መንግሥት፤ አብሮነት እንዲከተል፤ ትግሉን አሁን በአንድነት ማካሄድ የሚል ግንዛቤ ይዤ ነው።

የአንድነቱን ትግል ለማድረግስ፤ መነጋገር ያለባቸው እነማን ናቸው? ይህ ደግሞ ራሱን የቻለ ጉዳይ ነው። በኔ እምነት፤ መጀመሪያ አማራው በአንድ ላይ ሆኖ፤ አንድ አማራውን የሚወክልና የአማራው ትግል ተጠሪ አካል ማበጀት አለበት። ይህ አጠያያቂ አይደለም። እየተደረገም ነው። በርግጥ በምመኘው ፍጥነት እየሄደ አይደለም። አማራው የያዘውን ትግል ምንነት፣ የትግሉን ዕሴቶች፣ የትግሉን ግብ፣ የትግሉን የጉዞ መስመር፣ ከሌሎች ጋር ሊኖረው የሚፈልገውን የትብብርና የአብሮነት መሰላል፤ በግልጽ ማስቀመጥ አለበት።

በዚህ ቅንብሩ፤ ሌሎችን ወደ ትግል መጋበዝ ይጠበቅበታል። ሌሎች ደግሞ፤ ቀድመው የተደራጁ እንዳሉ ግልጽ ነው። ያልተደራጅ ወይንም በተለያየ የተቃውሞ ግቢ ያሉት ደግሞ፤ ወደ ፖለቲካ ትግል ስብስብ ተዋቅረው፤ በዚህ ትግል በባለቤትነት መሰለፍ መቻል አለባቸው። በትግሉ አብረው በመሰለፍ፤ የነገ ሕልውናቸውን አስተማማኝ ማድረግ ይችላሉ። አሁንም ይህ በገዥነት ያለው የትግሬዎቹ ቡድን ቢወድም፤ “እኛ ጠበቃ ሆነን ትግሬዎችን እናድናለን!” በማለት፤ መሰሪ የሆኑ የዚሁ አጥፊ የትግሬዎቹ ገዥ ቡድን መስራቾች በሆኑት በግደይ ዘርዓፅዮንና በአረጋዊ በርሄ የሚመራ፤ ትግሬዎችን ብቻ ያካተተ የትግሬዎች ጠበቃ ድርጅት አቋቁመው፤ በታጋዩ ሕዝብ መካከል፤ አለሁ እያሉ ያወናብዳሉ። ተመልከቱ፤ “አሁንም የትግራይ ሕዝብ ተበድሏልና፤ ከናንተ ብዙ እንፈልጋለን!” ነው የሚሉን። እኒህን መንጥረን እናውጣቸው፤ ወይንም በኋላ የሠሩትን ሠርተው፤ በጎን አጥንታችን ውስጥ የሰላ ሰይፋቸውን ሰክተው ወደ ጓዶቻቸው ሲሄዱ፤ ምርር ብለን፤ ከዱን ብለን እናልቅስ።

እንግዲህ የአንድነት ውይይቱ፤ አማራው ባንድ ገጽ፤ የኦሮሞ ወጣቶች ደግሞ በአንድ ገጽ፤ ሌሎች የተደራጁ የተጨቆኑ ወገኖች በአንድ ገጽ እያሉ፤ ወደ አንድ ስብስብ በመምጣት፤ ማድረግ ይቻላል። ይህ ብቻ አይደለም መንገዱ። የተለያየ መንገድ ሊኖር ይቻላል። እኔ የማቀርበው መፍትሔ ብዬ ያየሁትን ነው። አማራው አንድ ደረጃ ላይ ደርሷል። አኙዋኩም ሆነ ኦጋዴኑ፣ ሲዳማውም ሆነ አፋሩ፣ የተደራጀውን የአማራ ክፍል ቢቀርብና ቢያነጋግር፤ አጋር ማራቱ ነው። በአሁኑ ሰዓት፤ የኢትዮጵያ ድርጅት ብሎ ማንም ቢዘላብድ፤ ግአንዘብ ከመሰብሰብና ታጋልኩ እያለ ከመፎከር ሌላ፤ አንዲት ቅንጣት እርምጃ ወደፊት አይሄድም። ወሳኙ፤ የአማራ ወጣቶችና፤ አሁን በቦታው ያሉ ሌሎች ታጋይ ወጣቶች ናቸው። እኒህን የሉም ብሎ ወይንም በኔ ሥር ሆናችሁ ታጋሉ ብሎ የሚነሳ፤ በጀርባው የያዘውን ማወቁ ይጠቅማል።

Posted in እስከመቼ - ESKEMECHE | አስተያየት ያስቀምጡ