የአሁኑ የተለየ ነው፤

የአሁኑ የተለየ ነው፤

ሐሙስ፣ ሐምሌ ፯ ቀን፤ ፳ ፻ ፰ ዓመተ ምህረት ( 7/14/2016 )

እንዱዓለም ተፈራ  –  የእስከመቼ አዘጋጅ

በጎንደር እየተካሄደ ያለውን ሀቅ፤ ሁላችንም በተለያየ መልክ እየተከታተልን ነው። በኢትዮጵያ ያለው መንግሥት የማንና ምን አንደሆነ በግልጽ ታይቷል። ሕዝቡም የደረሰበትን የ”በቃኝ!” ደረጃ እያየን ነው። አሁን በፓልቶክና በደረገጽ፤ በሬዲዮና በቲቪ መወሰናችን ያበቃበት ሰዓት ነው። ይህ ትግል እስከዛሬ ከተደረጉት ማናቸውም ሕዝባዊ እንቅስቃሴዎች የተለየ ነው።

በአኝዋክ ዘመዶቻችን አልቀዋል። በኦጋዴን ዘመዶቻችን ረግፈዋል። በኦሮሚያ ዘመዶቻችን ተገድለዋል። በተለያየ መልክ ሕዝቡ ምሬቱን ገልጿል። ከፍተኛ መስዋዕትነት ክፍሏል። ይህ ሁሉ ተደማምሮ አሁን የተነሳውን ሕዝባዊ አመጽ ወልዶታል። አሁን፤ የእስከዛሬው ጥርቅም ብሶት ውጤት ነው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ፊት የተደቀነው። የአሁኑ የተለየ ነው።

በጎንደር የወልቃይትን ማንነት ይዞ የተነሳው ወገናችን ጥያቄ፤ የማንነት ብቻ ሳይሆን፤ የወራሪውን አምባገነን ወገንተኛ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር መንግሥት፤ የፖለቲካ ፍልስፍናና የአስተዳደር መመሪያ መሠረት የሚንድ ጥያቄ ነው። እናም የዚህን ወራሪ ገዥ ሕልውና በጥያቄ ውስጥ ያስገባ ነው። ስለዚህ መልሱ፤ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር ሞት ብቻ ነው።

በቪዲዮው እንደተመለከታችሁት፤ ወጣቱ የሥርዓት ጥያቄ አንግቧል፣ ኢትዮጵያዊነቱን በጩኸት ተናግሯል፣ ተገድሏል፣ ጠመንጃ ይዞም መልስ ሠጥቷል። ለዚህ ማብረጃ ለሌለው መነሳሳት፤ ለኛ የቀረበልን ጥያቄ፤ አብሮ ከሕዝቡ ጋር መቆም አለያም ከሕዝብ ጨፍጫፊው ወራሪ ወገንተኛ አምባገነን የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር ጋር መሰለፍ ነው? የቱን እንመርጣለን?

ይህ ወራሪ ገዢ ቡድን፤ እስካሁን እንዳደረገው ሁሉ፤ ለዚህ ሕዝባዊ መነሳሳት የሚሠጠው መልስ ግልጽ ነው። በሽምቅ ታጋይነቱ ወቅት ባነገበው፤ ሁሉን ነገር “እኛ” እና “እነሱ” ፍረጃው፤ የ”እኛ” ያልሆነውን ሁሉ፤ ጥያቄውን ከነመልዕክተኛው በጥይት! ነው። በጎንደር ብዙ ደም ይፈሳል። የሕዝቡ ብቻ ሳይሆን፤ የወራሪውም ወገን ደም ይፈሳል። ይህ ወራሪ፤ በሚችለው መንገድ ሁሉ፤ ጊዜ ለመግዛት ጥረት እያደረገ ነው። ሽማግሌዎችን ላከ። አልተሳካለትም። ወታደሩን ማጉረፍ ይዟል። ሕዝቡን ለመከፋፈል ይጥራል። መነሳሳቱን ለመቀልበስ እንድትረዳው፤ ሱዳን አካባቢውን እንድትወር ሊያደርግ ይችላል። አንዳንድ ሆዳሞችን በመግዛት፤ ሊካፋፍል ይጥራል። ይህን ሁሉ እስከዛሬ ሲያደርገው የነበረና የማያቆመው የማንነቱ ክን ነው። ከዚያም አልፎ የበለጠ ዘግናኝ ፀረ-ኢትዮጵያ የሆነ ተግባር ሊፈጽም ይችላል። ቁምነገሩ፤ ይህ ወራሪ እንዲህ ወይንም እንዲያ አደረገ እያልን መዘክዘኩ ላይ አይደለም። በሕዝቡ ወገን ምን ተደረገና፤ ምን ማደረግ ያስፈልጋል? የሚለው ላይ ማተኮሩ ላይ ነው።

ወጣቱ፤ ወራሪው ራሱ ባቀረበው መስፈርት፤ “ራስህ ተሰፈርበት!” ነው ያለው። “እኛ አማራ ነን!” ነው ያለው። ይህ ታዲያ ለምን ወንጀል ይሆናል? የወልቃይት ወገናችን፤ “እኛ አማሮች ነን!” አለ። ይህ ታዲያ የምን ወንጀል ነው? አዎ! ወራሪው መሬቱን እንጂ፤ በመሬቱ ላይ የሰፈርውን ወገናችንን አይፈልግም። ይህን ግን በቀላሉ ሊያካናውነው የሚችል አልሆነለትም። እንዲሳካለት፤ የዚያን አካባቢ ወገናችንን ገሎ መጨረስ አለበት። ይህ ነው እቅዱ። ለወራሪው የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር፤ ወልቃይትን አሳልፎ ለባለቤቶቹ መሥጠት ማለት፤ ሞት ማለት ነው። ፍጹም አያደርገውም። በጎንደር ያለው ወገናችን ደግሞ ከዚህ ንቅንቅ አይልም። ስለዚህ ይህ መነሳሳት ከእስካሁኑ የተለየ ነው።

በተጨማሪ፤ ደም ፈሷል። ሁላችን እንደምናውቀው ለፈሰሰው ደም ተጠያቂ ወራሪው ቡድን ቢሆንም፤ ከበሮ ራሷ ጩኻ ነውና፤ ተበደልኩ ብሎ የሚያላዝነው ወራሪው ነው። እዚህ ላይ፤ ይህ ሁሉ ሲፈጸም በሀገሪቱ ያለው መንግሥት ምን ላይ ቆሟል? ብለን እንጠይቅ። በመጀመሪያ ደረጃ፤ ከትግራይ የተላኩ የትግራይ ወታደሮች፤ እንዴት ብለው ነው ጎንደር ውስጥ ያለ አካባቢው አስተዳደር እውቅና፤ ሰተት ብለው ገብተው፤ የወልቃይት ኮሚቴ አባላትን አፍነው ሊወስዱ የደፈሩት? ይህን የሚያዘው፤ መቀሌ ላይ ተቀምጦ አባይ ወልዱ ነው። እንግዲህ፤ በሀገሪቱ አዛዥ ናዛዥ፤ የትግራዩ አስተዳደር ነው፤ ማለት ነው። ቀጥሎ ደግሞ፤ አንድን ወገን አማራ መሆን ወይንም አለመሆን ወሳኙ፤ መቀሌ ያለው አስተዳደር ነው ማለት ነው፡ ታዲያ፤ በሀገሪቱ ያለው የትግሬዎች መንግሥት ነው ማለት አይደለም? ለምን መጠማዘዝ ያስፈልጋል? ለምን መልመጥመጥ ያስፈልጋል። በኢትዮጵያ ያለው፤ የትግሬዎች መንግሥት ነው።

ቀደም ብሎ፤ ለምን “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር መንግሥት” ብለህ ትጠራለህ? የሚል ወቀሳ ከየአቅጣጫው ደርሶብኝ ነበር። እኔም ራሳቸውን በጠሩት ስም ነው የጠራኋቸው በማለት በተደጋጋሚ መልሼ ነበር። የጠሉኝ ቀጥለውበታል። ይሁንላቸው። ዛሬ ለይቶልኝ፤ በሀገራችን ያለው፤ የትግሬዎች መንግሥት ነው ብያለሁ። የዚህ መንግሥት መሠረቱ፣ ግድግዳው፣ ማገሩ፣ ጣራው ትግሬዎች ናቸው። ይሄን አይደለም ባይ፤ ያሳየኝና ልማር። በትግሬዎችና በአማራው መካከል ይህ መንግሥት ያስቀመጠው ቅርቃር፤ ለመቼውም የማይበርድና አደገኛ ሆኗል። ይህ መንግሥት ግን ግድ የለውም። የነገዎቹን ትግሬዎች ብቻ ሳይሆን፤ የዛሬዎቹንም አደጋ ላይ አስቀምጧቸዋል። በርግጥ ለዚህ ደንታ የለኝም ልል አልችልም። ሆኖም ግን፤ እስኪ መጀመሪያ ሀገራችንን በአንድነት ሁላችን ነፃ እናውጣና፤ ለተለየ አካባቢ ያለውን መልስ በኋላ እንሥጥ።

በተለይ በአማራው ላይ እስካሁን ያደረሰው በደል፤ የትም ቦታ የሌለና፤ ከሁሉም የከፋ ነው። በዘር ማጥፋት ወንጀል የሚያስጠይቅም ነው። አማራው ችሎ፤ ችሎ፤ አሁን በቅቶት ተነስቷል። ተነስቶ ደግሞ ኢትዮጵያዊ ነኝ እያለ ነው። እናም ያሁኑ የተለየ ነው። ይህን መነሳሳት ማንም ድርጅት እየመራው አይደለም። ሕዝባዊ ነው። የራሱ የሕዝቡ ልጆች ከጎኑ እየመሩት ነው። ይህን መነሳሳት ከድርጅት ጋር እያዛመዱ “እኔ አስነሳሁት!” ባይ ድርጅት ካለ፤ ከጠላት የከፋ አደገኛ ጠላት ነው። እናም ይህ መነሳሳት የተለየ ነው።

ይህ መንሳሳት ብዙ እንቅፋቶች አሉት። አደጋ አንዣብቦበታል። መሪዎቹን፤ ገዥው ወራሪ ለቅሞ ሊጨርሳቸው እያሰላ ነው። መነሳሳቱ ድርጅታዊ ጥንካሬው ሥሩ ሩቅ አይደለም። እናም ተከታታይ መሪዎች ማቅረቡና የወደፊት እቅድ ማዘጋጀቱ ላይ ችግር ሊያጋጥመው ይችላል። በርግጥ፤ ወራሪው በሚወስደው እርምጃ፤ ዕለት ከዕለት ጥንካሬ እያገኘ መሄዱና መጎልበቱ አይቀሬ ነው። ሆኖም ግን፤ የዛሬን አዳሩ፤ ወሳኝ የሆነው ድርጅታዊ ጥንካሬው፤ ያስጋኛል። በዚህ መነሳሳት የተሰለፉ ወገናችን፤ ለቆራጥነታቸው ጥያቄ ሊኖረን አይገባም። ያስፈለገውን ለመክፈል ለመዘጋጀታቸው ጥርጥር የለኝም። በአንጻሩ ግን፤ ወራሪው ለሚያጠምዳቸው ሤራዎችና ለሚጠቀምበት መሰሪ ተግባር፤ የተነሳሳው ወገናችን ምን ያህል ተዘጋጅቷል ነው?

ጎንደሬ ነኝ ባይ ሁሉ፣ አማራ ነኝ ባይ ሁሉ፣ ኢትዮጵያዊ ነኝ ባይ ሁሉ፤ ትልቅ ፈተና ከፊታችን ላይ ተጋርጧል። ፈተናው፤ “ይህን ሕዝባዊ መነሳሳት በሚያስፈልገው መንገድ ሁሉ መደገፍ!” ነው። ትግሉ ኢትዮጵያዊ ለመሆኑ ጥያቄ የለም። በኢትዮጵያዊነታቸው አምነው፤ “ኢትዮጵያዊ ነን!” እያሉ ነው የፎከሩት። አትድረሱብን ማለታቸውን፤ የተላኩ የትግራይ ወታደሮች በመግደል አስመስክረዋል። የተላኩት ወታደሮች፤ የትግራይን ገዥዎች ዓላማ ለማሳከት ከትግራይ የመጡ እንጂ፤ የኢትዮጵያን ሕዝብ ጥቅም ለማስከበር የመጡ የኢትዮጵያ ወታደሮች አይደሉም። ከየትም ይምጡ ከየት፤ እኒህ የኢትዮጵያ ሕዝብ ወታደሮች አይደሉም። እናም በኢትዮጵያ መንግሥት ወይንም ወታደሮች መካከልና በጎንደር ወገናችን መካከል እየተደረገ ያለ ፍልሚያ አይደለም። ይህ በትግራይ ወራሪዎችና በጎንደር የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን አልወረርም ባዮች መካከል እየተደረገ ያለ ፍልሚያ ነው። እናም ከእስከዛሬው የተለየ ነው።

ይህ ሊቆም የሚችል መነሳሳት አይደለም። ደም መፋሰሱ ብቻ ሳይሆን፤ ምሬቱ ከጫፍ የደረሰና ለመሞት የተዘጋጀ ወገናችን የተሰለፈበት ነው። እናም ወራሪው መልስ ሊሠጥበት የሚችል አይደለም። መልሱ ሕልውናውን መሰረዝ ነውና! ይሄን ደግሞ አያደርገውም። እናም የአሁኑ የተለየ ነው።

እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ነኝ ባይ፤ ይህ መነሳሳት “የኔ ነው!” ብሎ እንዲቆም እጠይቃለሁ። ይህ የሀገርን ሕልውና፣ የሕዝቡን አንድነት፣ የመኖርን እና የአለመኖርን ጥያቄ ያነገበ ጉዳይ ነው። እስከዛሬ በየቦታው በዚህ ወራሪ እየተገደለ በጉራው የተጣለው የአማራ ደም ጮኋል! የአኝዋኩ ደም፣ የኦሮሞው ደም፣ የኦጋዴኑ ደም፣ ተጣርቷል። አሁን ያልተነሳን፤ መቸም ቢሆን አንነሳም። ዛሬ የተነሱት ጩኸታቸው ከእስካሁኑ የተለየ ነው። የታሪክ፣ የሀገርና የትውልድ ጥሪ በየጆሮዎቻችን ላይ ደወሎቻቸውን አቃጭለዋል። መልሳችን ምንድን ነው?

ከተነሳሳው ወገናችን ጎን መቆሙ፤ የሕሊና ጓዳችንን ስለፈተሸ፤ የምንሠጠው መልስ፤ ማንነታችንን ይናገራል። አንብበን ፊታችንን ማዞር እንችላለን። ይህ የኔ ጉዳይ አይደለም ልንል እንችላለን። ትምህርቴን ልጨርስ፣ ሀብቴን ላከማች፣ ጉዳዬን ልጨርስ ማለት እንችላለን። ድሮም ሆነ አሁን፤ ጠላት ሲመጣ፤ አብረው ከጠላት የሚወግኑ ሆዳሞች አሉን፤ ነበሩንም። አሁንም ሆዳም ነኝ ብሎ፤ ለቀፈት ማስብ ይቻላል። “ሀገር ቤት ትልቅ ቤት ልሠራ ነውና ከዚህ አልገባም”፤ ማለትም ይቻላል። ባንዳዎች አዲስ አይደሉም። ሆድ አደሮች አዲስ አይደሉም። አርበኞችን ከጀርባቸው የወጉ በታሪካችን ሞልተዋል። ይህ ጥያቄ ለየግላችን የመጣ ነው። አንቺ፣ እንተ፣ እርስዎ፣ ምን ይላሉ። ይህ የግል መልስ ይፈልጋል። የት ላይ ቆመዋል?